የ2017 ዓ.ም የኢትዮጵያ ዋንጫ የሁለተኛ ዙር ጨዋታዎች በዛሬው ዕለት በአዲስ አበባ አበበ ቢቂላ ስታድየም መደረግ ጀምረዋል።
በቀዳሚነት ከረፋድ 4:00 ጀምሮ በተደረገው ጨዋታ የአንደኛ ሊግ ተሳታፊ የሆነው ሱሉልታ ክፍለ ከተማ የፕሪሚየር ሊጉን ተሳታፊ ወልዋሎ አዲግራትን አሸንፏል።
በጨዋታው ሁለተኛ ደቂቃ ላይ ኪያ ወርቁ ያስቆጠረው ግብ ሱሉልታ ክፍለ ከተማን ለዘጠኝ ያህል ደቂቃዎች መሪ ማድረግ ችሎ ነበር።
ጨዋታው 11ኛ ደቂቃ ላይ ሲደርስ ግን ኤፍሬም ኃይለማርያም ወልዋሎ አዲግራትን አቻ አድርጓል።
- ማሰታውቂያ -
መደበኛው የጨዋታ ክፍለ ጊዜ ተጨማሪ ግብ ባለማስተናገዱ ወደ መለያ ምት አምርቶ ሱሉልታ ክፍለ ከተማ 3 – 0 በማሸነፍ የመጨረሻ አስራ ስድሰቱን ተቀላቅሏል።
ሱሉልታ ከተማ በሶስተኛው ዙር ከመቻል እና አዲስ አበባ ከተማ አሸናፊ ጋር ጨዋታውን ያደርጋል።
ቀትር 7:00 ጀምሮ በተደረገው ጨዋታ የከፍተኛ ሊጉ የምድብ ሀ መሪ ሸገር ከተማ ቦሌ ክፍለ ከተማን በመርታት ቀጣዩን ዙር ተቀላቅሏል።
በጨዋታው 18ኛ ደቂቃ ላይ ሰይፈ ዛኪር ሸገርን መሪ ያደረገ ግብ ሲያስቆጥር ቦሌ ክፍለ ከተማዎች ከ20 ደቂቃዎች በኋላ ዑመድ ኦፒቲ ባስቆጠረው ግብ ወደ ጨዋታው ተመልሰዋል።
የመጀመሪያውን አጋማሽ በ1 – 1 ውጤት የፈፀመው የቀትሩ ጨዋታ 53ኛው ደቂቃ ላይ ሌላ ግብ አግኝቷል።
ምስጋናው ሚልኪያሰ የሁለተኛው አጋማሽ ከተጀመረ 8 ደቂቃዎች በኋላ ሸገር ከተማን ዳግም መሪ ሲያደርግ በ81ኛው ደቂቃ ላይ ደግሞ ያሬድ መኮንን 3ኛው ግብ ከመረብ አሳርፏል።
ከያሬድ መኮንን ግብ መቆጠር ሁለት ደቂቃዎች በኋላ ቦሌ ክፍለ ከተማዎች በጁንዲ ሀጂ አማካይነት ግብ አስቆጥረው በቀሩት ደቂቃዎች ዳግም አቻ ለመሆን ቢጥሩም ሳይሳካላቸው ቀርቷል።
ሸገር ከተማ በቀጣይ ዙር የኢትዮ ኤሌክትሪክ እና ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ጨዋታ አሸናፊ ጋር ይጫወታል።
9:30 ጀምሮ ሁለቱን የፕሪሚየር ሊግ ክለቦች ወላይታ ድቻ እና መቀሌ 70 እንደርታ ያገናኘው ጨዋታ በ2009 የውድድሩ ሻምፒዮን አሸናፊነት ተጠናቋል።
ሙሉ ዘጠና ደቂቃው ግብ ሳያስተናግድ በተጠናቀቀው ጨዋታ አላፊውን ለመለየት ወደ መለያ ምት አምርቶ ወላይታ ድቻ 3 – 1 በማሸነፍ ወደ ቀጣዩ ዙር መቀላቀሉን አረጋግጧል።
የዓምና የፍፃሜ ተፋላሚ የሆኑት የጦና ንቦቹ በቀጣይ ዙር የአዳማ ከተማ እና ቦዲቲ ከተማን አሸናፊ ይገጥማሉ።
የኢትዮጵያ ዋንጫ የመጀመሪያ ዙር ጨዋታዎች በነገው ዕለትም ቀጥለው ሶስት ጨዋታዎች በአዲስ አበባ አበበ ቢቂላ ስታድየም ላይ ይደረጋሉ።
ረፋድ 4:00 ላይ ድሬደዋ ከተማ ከአርባምንጭ ከተማ ፤ ቀትር 7:00 ላይ ኢትዮጵያ መድኅን ከአርባምንጭ ከተማ እንዲሁም 9:30 ላይ ሀዋሳ ከተማ ከቅዱስ ጊዮርጊስ ጋር ጨዋታቸውን ያደርጋሉ።


