የኢትዮጵያ ስፖርት ጋዜጠኞች ማህበር የክለቦች ደንብን ያልተከተለ የገንዘብ ክፍያን ተከትሎ በሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ የስፖርት ጋዜጠኞች በሚል በጠቀሰው ጉዳይ ላይ ማብራሪያ ጠይቋል።
በወቅቱ በተሰጠው መግለጫ ስማቸው ያልተጠቀሰ ሶስት የስፖርት ጋዜጠኞች በጉዳዩ ላይ እጃቸው አለበት ተብሎ መነገሩ ይታወሳል።
የስፖርት ጋዜጠኞች ማህበር ያወጣው ሙሉ መግለጫ እንደሚከተለው ቀርቧል።
“የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ አ.ማ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ተሳታፊ ከለቦች “የህገ-ወጥ” የገንዘብ ዝውውር እና ከፍያ ጋርበተያያዘ የካቲት 20፣ 2017 ዓም ለመገናኛ ብዙኃን ባለሙያዎች ጋዜጣዊ መግለጫ ሰጥቶ ነበር፡፡
- ማሰታውቂያ -
አከሲዮን ማህበሩ በሊጉ የክለቦች ህገ-ወጥ የገንዘብ ዝውውር እና ከፍያ ጋር በተያያዘ ያወጣው ሪፖርት እና ቅጣት ገና በሂደት ላይ ያለ ቢሆንም የኢትዮጵያ ስፖርት ጋዜጠኞች ለአመታት ሲያነሱት፣ መፍትሄ ያሻዋል በሚልም ሲጮሁለት የከረመ ጉዳይ በመሆኑ ጅምሩን የኢትዮጵያ ስፖርት ጋዜጠኞች ማህበር ያበረታታል፡፡ ፍትሃዊ እና ግልጽ አሰራር በእግርኳሱ ውስጥ እንዲኖርም ማህበራችን ከአክሲዮን ማህበሩ ጋር በጋራ ለመስራት ዝግጁ ነው፡፡
ይሁን እንጂ የካቲት 20፣2017 በጠራው ጋዜጣዊ ጉባኤ 3 (ሶስት) የስፖርት ጋዜጠኞች አሉ በሚል ያወጣውን መረጃ ዛሬም ድረስ ብንጠብቅም አክሲዮን ማህበሩ ይፋ አላደረገም፡፡ የስፖርት ጋዜጠኞች እንደማንኛውም ዜጋ ካጠፉ የማይጠየቁበት ምከንያት እንደሌለ ማህበራችን በፅኑ ያምናል፡፡ ለዚህም ነው ዛሬም ድረስ በጉዳዩ ላይ የኢትዮጵያ ስፖርት ጋዜጠኞች ማህበር ዝምታን የመረጠው::
ጉዳዩ የስፖርት ጋዜጠኞችን ስም እና ዝና የሚያጎድፍ፣ ስነልቦናዊ ጫናም የፈጠረ ነው፡፡ አከሲዮን ማህበሩ መረጃው አለኝ ካለ ማውጣት፤ ካልሆነ ደግሞ ዝም ማለት ሲገባው በዚህ መልኩ በእንጥልጥል በቀረ ሀሳብ “ሀሜት” በሚመስል መልኩ መረጃን ማውጣት ተገቢ መስሎ አልታየንም፡፡
ስለሆነም የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ አክሲዮን ማህበር ማብራሪያ እንዲሠጠን በትህትና እንጠይቃለን፡፡”


