የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ እግር ኳስ ደጋፊዎች ማህበር ክለቦችን ለመደገፍ ያለመ ነው ያለውን የስትራቴጂክ አጋርነት ስምምንት ከአሪፍ ፔይ ጋር አድርጓል።
በአዲስ አበባ ስታድየም በተካሄደው የአጋርነት ስምምነት መርሐግብር የአሪፍ ፔይ የቢዝነስ ዴቬሎፕመንት እና የፓርትነርሺፕ ዳይሬክተር አቶ ግሩም ጌታቸው እና የደጋፊዎች ማህበሩ ፕሬዚዳንት አቶ ደነቀው በሪሁን ፈርመዋል።
ስምምነቱ የክለብ ደጋፊዎች ምዝገባ ፣ የትኬት ሽያጭ ፣ የማልያ ሽያጭ የመሳሰሉትን እና ሌሎች የገንዘብ ዝውውሮችን በቀለለ እና በዲጂታል መንገድ ለማከናወን የሚያስችል ነው ተብሏል።
ይህ የስትራቴጂክ አጋርነት ስምምነት ለኢትዮጵያ እግር ኳስ የትንሳኤው መሰረት ነው ብለን እናስባለን ሲሉ የተናገሩት አቶ ግሩም ጌታቸው ናቸው።
- ማሰታውቂያ -

አክለውም ክለቦች አሁን ላይ እየሄዱበት ካለው መንገድ ጋር የጥቅም ግጭት አያመጣም ፤ አሪፍ ፔይ ከባንኮች ጋር በጋራ ይሰራል ገንዘቡ በአንድ መንገድ ተሰብሰቦ ክለቡ በመረጠው የባንክ አካውንት ገንዘቡ ይገባል ብለዋል።
“ኢትዮጵያ ውስጥ እግር ኳስ እንወዳለን። ግን ዕድገት እያመጣ አይደለም እንደውም ወደ ቁልቁለት እነተጓዘ ነው። እንደ ተቋም እግር ኳሱን መደገፍ አላማችን ነው።”
“ይሄንን እግር ኳስ ዲጂታላይዝ ማድረግ ከቻልን የምንጠብቀውን ክለቦች ራሳቸውን እንዲችሉ ማድረግ እንችላለን። ደጋፊ አላቸው ነገር ግን ከደጋፊዎቻቸው ገንዘብ የሚሰበስቡበት መሳሪያ የላቸውም።”
“ይህን መሳሪያ ከደጋፊ ማህበር ጋር ተዋህደን ሲስተም ፈጥረን እና አዘጋጅተን የክፍያ መንገዱን ማሳለጥ እስከቻልን ድረስ ክለቦች ራሳቸውን መቻል ይችላሉ የሚል ሀሳብ በመያዝ ብሎም ደግሞ የኢትዮጵያን እግር ኳስ ብሎም ደግሞ ክለቦችን ለመደገፍ ነው ፤ ይህንን የአጋርነት ስምምነት ያደረግነው።”
እግር ኳስ ካለ ፋይናንስ ምንም ነው ያሉት አቶ ደነቀው በሪሁን በበኩላቸው እንደ ደጋፊ ክለቦች ገንዘብ የሚያገኙበት መንገድ ማመቻቸት አለብን የስምምነቱ ዋና አላማም ይህ ነው ብለዋል።
“ደጋፊ ማለት ምን ማለት ነው ክለቡን የሚደግፍ ማለት ነው። አብዛኞቻችን አሁን ያለንበት ሁኔታ ግን ከክለቡ ነው የምንደግፈው እና ስለዚህ የደጋፊዎች ጥምረት ዓላማው የተቋቋመበት ደጋፊ ማህበራትን በተለያየ መልኩ ማጠናከር ነው።”
“ስለዚህ ከዚህ ደግሞ ደጋፊ ማህበራት በቀላሉ ገንዘብ አምንጭተው ለክለቦቻቸው ገንዘብ የሚሰጡበት መልኩን ፕላትፎርም ማዘጋጀት አለብን ብለን ጥምረቱ ባስለማው ለደጋፊ ማህበራት በነፃ የሚሰጥ አሪፍ ፔይን እና ከጀርባው የዴሊቨሪ አገልግሎት ያለው መተግበሪያ ሰርተን ነው ወደዚህ ስራ የመጣነው። ይሄ ለደጋፊ ማህበራት በሙሉ በነፃ የሚሰጥ ነው”
ይህ ስምምነት በክለቦች የተመዘገቡ ደጋፊዎችን ቁጥር በማሳወቅ እና በመጨመር ለሌሎች አጋር ስፖንሰሮችም ጭምር ዳታዎችን ማቅረብ የሚቻልበት ነው ሲሉ ተናግረዋል።
“ብዙ ጊዜ ምንድነው የምንቸገረው ለምሳሌ አርባምንጭ ከተማ ምን ያህል ደጋፊ አለው ቢባል ፤ ድሬዳዋ ከተማ ምን ያህል ደጋፊ አለው ቢባል አዳማ ከተማ ምን ያህል አይታወቅም። አሁን ግን መረጃ ይኖረናል። በሚቀጥለው አመትም ይሄን መረጃ ላላወጡም በኤስ ኤም ኤስ ቴክስት እየላክን ደጋፊዎች መታወቂያቸውን እንዲያድሱ እንዲያወጡ እናደርጋለን ማለት ነው።”
ማህበሩ የተቋቋመው እግር ኳስን በእግር ኳስ ቋንቋ ብቻ እንደግፋለን ብለን ነው ፤ ደጋፊ ማህበራት የተቋቋሙትም ክለቦችን ለመደገፍ ነው ፤ ተባብረን ከሰራን የሀገራችንን እግር ኳስ መለወጥ እንችላለን ሲሉ አቶ ደነቀው ተናግረዋል።
የአጋርነት ስምምነቱ በየዓመቱ እየታደሰ የሚቀጥል ስለመሆኑን በመግለጫው ተጠቅሷል።
የሁሉም ክለብ ደጋፊዎች ለዚህ ተብሎ ለሁሉም ክለቦች የተዘጋጀውን መተግበሪያ ላይ ካሉበት ሆነው መጠቀም እንደሚችሉም ተገልጿል።


