በቤትኪንግ ኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ የ23ተኛ ሳምንት መርሐግብር በሁለተኛው ዕለት ምሽት 12 ሰዓት ላይ በተደረገ ጨዋታ ድሬዳዋ ከተማ ኢትዮ ኤሌክትሪክን 2ለ0 በሆነ ዉጤት ማሸነፍ ችሏል።
በዉጤት ደረጃ ለሁለቱም ክለቦች እጅግ ወሳኝ በነበረዉ የሁለቱ ክለቦች ጨዋታ የአስራት አባተ ቡድን ድሬዳዋ ከተማ በከፍተኛ የማጥቃት እንቅስቃሴ ተከላካዮቹን ይበልጥኑ ወደ ሜዳዉ የመሐል ክፍል አስጠግቶ ሲጫወት ፤ በተቃራኒው ኢትዮ ኤሌትሪክ በጥብቅ መከላከል አልፎ አልፎ በሚገኙ አጋጣሚዎች ለመጫወት ሲጥሩ ተስተውሏል።
በዚህም ገና በ1ኛዉ ደቂቃ ቢኒያም ጌታቸዉ በቀጥታ ከሳጥን ውጭ ጥሩ ኳስ ሞክሮ የነበረ ቢሆንም ለጥቂት ኳሷ ወደ ዉጭ ወጥታበታለች። በ21ኛዉ ደቂቃ ላይ ደግሞ በድጋሚ ቢኒያም ጌታቸዉ ከመሐል ክፍሉ ከኤልያስ አህመድ የተቀበለዉን ኳስ በጥሩ ቅልጥፍና ገፍቶ ሳጥን ውስጥ ከደረሰ በኋላ ወደ ግብ ሞክሮ የነበረ ቢሆንም ግብ ጠባቂዉ ካክፓ አቶ እንደምንም ኳሷን አዉጥቶታል።
- ማሰታውቂያ -
የሁለቱ ክለቦች ጨዋታ ጥሩ የሚባል እንቅስቃሴን ቢያስመለክትም በሙከራ ረገድ ግን እጅግ ደከም ያለ የመጀመሪያ አጋማሽ ነበር ክለበቹ ያሳለፉት ፤ በተለይ ኤሌትሪኮች በኢብራሂም ከድር እና አብዱራህማን ከድር አማካኝነት ካደረጓቸዉ ጥቂት ሙከራዎች ዉጭ በአጋማሹ አደጋ ለመፍጠሩ ሲቸገሩ ተስተውሏል። በተለይ ግን አማካዩ አብነት በ22ተኛዉ ደቂቃ ላይ ከሳጥን ዉጭ ሞክሮ ወደ ግብ የላካትን ኳስ ግብ ጠባቂዉ ዴንኤል ተሾመ ያወጣት አጋጣሚ ተጠቃሽ ነበረች።
ከዕረፍት መልስ በንፅፅር የማጥቃት ሀይላቸዉን አጠንክረዉ የቀጠሉት ድሬዳዋዎች በ51ኛዉ ደቂቃ ላይ ጥሩ ሙከራ ማድረግ ችለዋል። በዚህም ቢኒያም ጌታቸዉ ከቀኝ በኩል ያቀበለዉን ኳስ ቻርልስ ሙሴጌ በቀጥታ ወደ ግብ ሞክሮ የነበረ ቢሆንም ግብ ጠባቂዉ ኳሷን እንደምንም አውጥቷታል።
በ62ተኛዉ ደቂቃ ላይ የተገኘዉን የቅጣት ምት ኳስ የመስመር ተጫዋቹ ጋዲሳ መብራቴ በቀጥታ ወደ ግብ ሞክሮ የነበረ ቢሆንም በዕለቱ ድንቅ የነበረዉ የኤሌትሪኩ የግብ ዘብ እንደምንም አውጥቶበታል። አልፎ አልፎ ከሚገኙ የመልሶ ማጥቃት አጋጣሚዎች ዉጭ እምብዛም በሙከራ ረገድ ስል ሁነዉ ያልቀረቡት ኤሌክትሪኮች የጨዋታው ደቂቃ እየገፋ በመጣ ቁጥር በድሬዎች ብልጫ ሲወሰድባቸዉ ተመልክተናል።
መደበኛዉ ዘጠና ደቂቃ ሊጠናቀቅ አራት ያህል ደቂቃዎች ሲቀሩት ግን ብርቱካናማዎቹ በ86ተኛዉ ደቂቃ ግብ ማስቆጠር ችለዋል። በዚህም በዕለቱ ጥሩ ሲንቀሳቀስ የነበረዉ አጥቂዉ ቢኒያም ጌታቸው ከሙህዲን ሙሳ የተቀበለዉን ኳስ ወደ ግብነት በመቀየር ክለቡን መሪ ማድረግ ችሏል።
በጨዋታው የመጨረሻ ደቂቃ ላይ ግብ አስቆጥረዉ ጨዋታውን መምራት የጀመሩት ብርቱካናማዎቹ በድጋሚ በ90ኛዉ ደቂቃ ላይ ተጨማሪ ግብ በሱራፌል ጌታቸዉ አማካኝነት አስቆጥረዉ ጨዋታውን 2ለ0 በሆነ ዉጤት ማሸነፍ ችለዋል።