በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ በቅርብ ዓመታት ላዬ አስደናቂ የሜዳ ላይ እንቅስቃሴ በማሳየት ላይ ካሉ ተጫዋቾች አንዱ ነው።
በክለብ ያሳየው ብቃትም የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድንን ማልያ ለብሶ እንዲጫወትም አድርጎታል። በቀጣይ ዓመታት በሊጉ ከሚነግሱ ፤ በሌሎች ሊጎች ከሚታዩ እና ለዋልያዉ በተስፋ ከሚጠበቁ ተጫዋቾች መካከል ከፊት የሚገኘው ነው።
ለትውልድ ከተማው ክለብ በመጫወት ላይ የሚገኘው ብሩክ ማርቆስ………ውድ የሀትሪክ ስፖርት ድህረገጽ ተከታታዮች ከተስፈኛው ብሩክ ማርቆስ ጋር ቆይታ አድርገናል።
የሀድያ ብሔረሰብ የዘመን መለወጫ በዓል “ያሆዴ”ን አስታኮ የሚደረገው “ያሆዴ ካፕ” የእግርኳስ ውድድር ዛሬ ለደረሰበት ትልቁን ድርሻ አበርክቶለታል።
- ማሰታውቂያ -
ከ2015 የውድድር ዘመን ጀምሮ በከቤራዎቹ ማልያ በመድመቅ ላይ ያለው ብሩክ የዘንድሮ ሁሉም አስሩንም የሊግ ጨዋታዎች ጨምሮ በአጠቃላይ 66 የሊግ ጨዋታዎችን በክለቡ ማልያ ለብሶ በሊጉ ተጫውቷል።
ከእግርኳስ አጀማመሩ እስከ ወደ ፊት ህልሙ ፤ ስለ ሀድያ ሆሳዕና የዘንድሮው ድንቅ ግስጋሴ ፤ ስለ ኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን እንዲሁም ዛሬ ከመቻል ጋር ስለሚያደርጉት ተጠባቂ ጨዋታ ሀሳቡን አጋርቶናል።
ሀትሪክ :- የእግር ኳስ አጀማመርክ ምን አይነት ገፅታ ነበረው ?
ብሩክ ማርቆስ :- ያው እግር ኳስን (ይህ ምላሽ በበርካታ ኢትዮጵያውያን ተጨዋቾች ዘንድ የተለመደ ምላሽ ቢመስልም በወቅቱ ሌሎች አማራጮች ሰላልነበሩ) እንደ አብዛኛው ኢትዮጵያዊ በሰፈር ውስጥ ጨርቅ ኳስ በመጫወት ነበር የጀመርኩት ። ከልጅነቴ ጀምሮ የእግር ኳስ ፍቅር በውስጤ ነበረ እና ፍቅሬን ለማስታገስም በሰፈር እና በትምህርት ቤቶች ውድድሮች ላይ በመሳተፍ ነው የጀመርኩት ፤ ከዛም በፕሮጀክት ደረጃ በሆሳዕና ከተማ “ሴች ዱና” በሚባል የፕሮጀክት ቡድን ውስጥ በሰይፈዲን(ሰይፎ) አማካይነት ከእድሜ እኩዮቼ ጋር እንሰራ ነበር።
ሀትሪክ :- ክለብ የገባህበትን አጋጣሚ አስታውሰኝ እስኪ ?
ብሩክ ማርቆስ :- ለመጀመሪያ ጊዜ ክለብ የገባሁት በ2014 ዓ.ም ላይ ነበር ። በወቅቱ በብሔራዊ ሊግ የሚሳተፈው “ሀዲያ ሌሞ” ክለብ የሙከራ ጊዜ አዘጋጅቶ ነበር እና ያን የሙከራ ጊዜዬን በተሳካ ሁኔታ አጠናቅቄ ቡድኑን መቀላቀል ችያለሁ ። ሀዲያ ሌሞ ቤት የነበረኝ የአንድ ዓመት ቆይታ ለእኔ በጣም ጥሩና ብዙ ነገሮችን የተማርኩበትም ነበር ማለት እችላለሁ ።
ከዛም በመቀጠል በየዓመቱ መስከርም ወር መጀመሪያ ላይ የሀዲያ ብሔር ዘመን መለወጫ “ያሆዴ” በዓል በደማቅ ሁኔታ ይከበራል ። የበዓሉ ማድመቂያ ከሆነ ነገሮች አንዱ በክረምት ወራት የሚካሄድ “ያሆዴ ካፕ” ውድድር ሲሆን ይህ ውድድር የሚካሄደውም በዓሉ ከመድረሱ በፊት ቀደም ብሎ ባለው ክረምት ላይ ነው ።
በዛ ዓመት በነበረው “ያሆዴ ካፕ” ውድድር ላይ “ወየዳ” ቡድንን ወክዬ በመጫወት ከቡድን ጓደኞቼ ጋር የውድድሩ ሻምፒዮን መሆን ችለናል ። በፍፃሜው ጨዋታ ቀን በወቅቱ የሀዲያ ሆሳዕና ዋና አሰልጣኝ በመሆን የተሾሙት አሰልጣኝ ያሬድ ገመቹ ሆሳዕና አቢዬ ኤርሳሞ መታሰቢያ ስታዲየም ተገኝተው የፍፃሜውን ጨዋታ ከተመለከቱ በኃላ የሙከራ እድል ሰጡኝ ።
በሙከራው ወቅት በነበረኝ ተስፋ ሰጪ እንቅስቃሴ ምከንያት ቀጥታ ወደ ሀዲያ ሆሳዕና ዋናው ቡድን በአሰልጣኝ ያሬድ ገመቹ አማካይነት በ2015 ዓ.ም መቀላቀል ችያለሁ ። በዚህ አጋጣሚ አሰልጣኝ ያሬድ ገመቹ አምኖብኝ ዕድል ስለሰጠኝ ከልብ አመሰግናለሁ ማለት እፈልጋለሁ ።
ሀትሪክ :- ሀድያ አካባቢ ያለው የእግርኳስ ፍቅር ምን ይመስላል ?
ብሩክ ማርቆስ :- ሀዲያ ዞን ውስጥ ሴቱም ወንዱም ለእግር ኳስ ስፖርት ያለው ፍቅር የተለየ ነው ። የሚገርምህ ሀዲያ ሆሳዕና ጨዋታ ሲኖረው በከተማው የተለያዩ ቦታዎች ላይ የክለቡ ባንዲራ ተሰቅሎ ትመለከታለህ ፣ የሊጉ የውድድር ቅርፅ በሜዳ እና ከሜዳው ውጪ በነበረ ወቅት ሀዲያ ሆሳዕና ጨዋታ ሲኖረው ስታዲየም ውስጥ እና ስታዲየም ዙሪያ የተገኘውን ሰው አይተህ ቤት ውስጥ ማን ቀረህ? ብለህ እራስህን ልትጠይቅ ትችላለህ።
ዲኤስቲቪ ከመጣ በኋላም ሀዲያ ሆሳዕና ጨዋታ ካለው ዲኤስቲቪ ቤቶች ተጨናንቀው ማየት የተለመደ ነው ።
ሆሳዕና አቢዬ ኤርሳሞ መታሰቢያ ስታዲየም ብትሄድ የክረምት ውድድሮችን ለማየት የሚሄደውን የሰው ብዛት ይገርምሀል ። የሀዲያ ህዝብ ለእግር ኳስ አልፎም ለሀዲያ ሆሳዕና እግር ኳስ ክለብ ምን ያህል ፍቅር እንዳለው ክለቡ ጨዋታ ባለበት ቦታ ሁሉ በየከተማው እየዞረ የሚደግፈውን የደጋፊ ብዛት ማየት ነው ።
ባለፈው ክረምት ደቡብ አፍሪካ በሄድንበት አጋጣሚ ስታዲየም ውስጥ የነበረው የተመልካች ቁጥር ብዛት አይተሀል መቼም ። ያን ሁሉ ተመልካች ያየ ሰው ኢትዮጵያ ውስጥ ለዛውም ሆሳዕና እንጂ ደቡብ አፍሪካ ነበር ብትለው ላያምን ይችላል ። በአጠቃላይ ለእግር ኳስ የተለየ ፍቅር ካለው ማህብረሰብ ውስጥ በመፈጠሬ እድለኛም ደስተኛም ነኝ ።
ሀትሪክ :- በፕሮጀክትም ሆነ ወደ ክለብ ስትቀላቀል የቤተሰብክ ድጋፍ ምን ያህል ነበር ?
ብሩክ ማርቆስ :- ያለ ፈጣሪና ቤተሰብ እገዛማ እዚህ ጋር መገኘት ፈፅሞ የሚታሰብ አይደለም ። ቤተሰብ ህልሜን እንድኖር ባያግዘኝ ፈጣሪም ባይረዳኝ እዚህ እገኛለሁ ማለት ለእኔ ድፍረት ነው ። በዚህ አጋጣሚ ከፈጣሪ በመቀጠል ቤተሰቦቼን ላመሰግናቸው እወዳለሁ ።
ሀትሪክ :- በእግር ኳስ ምርጡ ጓደኛክ ማነው ?
ብሩክ ማርቆስ :- ሀዲያ ሆሳዕና ውስጥ ካሉ ከታዳጊ እስከ ሲነየር ተጨዋቾች ድረስ ጥሩ ግንኙነት አለኝ ። ለእኔ ሁሉም ምርጥ ጓደኞቼ ናቸው ።
ሀትሪክ :- የሀድያ ሆሳዕና የዘንድሮው የውድድር ዘመን ውጤታማነት ሚስጥር ምንድነው ማለት ይቻላል ?
ብሩክ ማርቆስ :- የውጤታማነታችን ሚስጥር አንድነታችን ነው ። እግር ኳስ የህብረት ስራ ነው ። ሜዳ ውስጥም ከሜዳ ውጭም ከተባበርክና ለአንድ ዓላማ ከቆምክ ስኬታማ መሆን ትችላለህ ።
ሀትሪክ :- የዘንድሮው ፉክክር ካለፉት አመታት ጋር ሲነፃፀር ከባድ ወይስ ….
ብሩክ ማርቆስ :- ዘንድሮ የጨዋታዎች ቁጥር ከፍ ብሏል ። ስለዚህ ጫና አለው ። አራት ቡድኖች ወደ ታችኛው ሊግ ስለሚወርዱ ሁሉም ቡድኖች ሁሉንም ጨዋታዎች በጥንቃቄ ነው የሚጫወቱት ።
ሌላው ዳግም ወደ ሊጉ ያደጉት አርባምንጭ ከተማና ኢትዮ ኤሌክትሪክም ጠንካራ ተፎካካሪ ሆነው ነው የተመለሱት ። ከአራት ዓመታት በኃላ ዳግም ወደ ሊጉ የተመለሱት ሶስቱ የትግራይ ቡድኖችም ብንመለከት በጣም ጠንካራ ናቸው ። ሰለዚህ ሊጉ ጥሩ ፉክክር የሚያሳየን ፈታኝ ዓመትም ይመስለኛል ።
ሀትሪክ :- ቀጣይ ዕቅድክ ምንድነው ?
ብሩክ ማርቆስ :- ሀገሬን በአህጉራዊና በዓለም አቀፋዊ ውድድሮች ላይ ከመወከል ባለፈ ውጤታማ እንድትሆን ከቡድን ጓደኞቼ ጋር በመሆን የበኩሌን አስተዋጽዖ ማድረግ እና አለፍ ሲልም ከሀገር ውጭ ባሉ ክለቦች የመጫወት እቅድ አለኝ ። ለዛም በእየለቱ ጠንክሬ እየሰራሁ እገኛለሁ ።
ሀትሪክ :- ብሔራዊ ቡድኑ ውጤታማ እንዲሆን ምን መደረግ አለበት ትላለህ ?
ብሩክ ማርቆስ :- የብሔራዊ ቡድናችን ውጤት ማጣት ችግር ዛሬ የመጣ ነው ብዬ አላስብም ። ባለፉት ዓመታትም የነበረ ነው። ድንገት ብልጭ ብሎ የሚጠፉ ስኬቶች አልፎ አልፎ ቢኖሩም በተከታታይ በአህጉራዊና አለም አቀፍ ውድድር ላይ የሚፎካከር ጠንካራ ብሔራዊ ቡድን ግን አልነበረንም ።
ይህንን ችግር ለመቅረፍ የተጠናከረ ሀገራዊ ስራ መሰራት አለበት ብዬ አስባለሁ ። ለአብነት ሁሉም ክለቦች ወጣት ቡድኖቻቸው ላይ በደንብ ትኩረት ሰጥተው መስራት አለባቸው ። ጠንካራ ወጣት ቡድን ያለው ክለብ ጠንካራ ዋና ቡድን ይኖረዋል ። የጠንካራ ዋና ቡድኖች ውጤት ጠንካራና ተፎካካሪ ብሔራዊ ቡድን ይፈጥራል የሚል እይታ ነው ያለኝ ።
ሀትሪክ :- ከሀድያ ሆሳዕና ጋር አሁን ላይ ያለህ ኮንትራት እስከ መቼ የሚቆይ ነው ?
ብሩክ ማርቆስ :- አሁን ላይ ከሀዲያ ሆሳዕና ጋር ያለኝ ኮንትራት በዚህ ዓመት መጨረሻ ይጠናቀቃል ።
ሀትሪክ :- በሊጉ ከመሪው በሁለት ነጥብ ብቻ ርቀት ላይ ነው የምትገኙት ፤ በኢትዮጵያ ዋንጫም የመጨረሻ አስራ ስድስቱን ተቀላቅላቸኋል። በዓመቱ መጨረሻ ምን ለማሳካት አቅዳችሁ እየሰራችሁ ነው ?
ብሩክ ማርቆስ :- በኢትዮጵያ ዋንጫም በሊጉም ከዓምናው የተሻለ ውጤት ለማምጣት እንደ ክለብ እቅድ አለን። እቅዳችንን ለማሳካትም ጠንካራ ስራ እየሰራን እንገኛለን ።
ሀትሪክ :- ከሀገር ውስጥ ተጫዋቾች አርዓያዬ የምትለው ማነው ?
ብሩክ ማርቆስ :- በጣም በዙ ናቸው ። ለምሳሌ አስራት መገርሳ ፣ አዲስ ህንፃ ፣ ጋቶች ፓኖም… በእኔ ቦታ ከተጫወቱ እና እየተጫወቱ ያሉ እንደ አርዓያ የምወስዳቸው ኢትዮጵያዊያን ተጫዋቾች ናቸው ።
ሀትሪክ :- ኳስ ተጫዋች ባትሆን ኖሮ በምን ሙያ ትሰማራ ነበር ?
ብሩክ ማርቆስ :- ከልጅነቴ ጀምሮ ራሴን ከኳስ ተጫዋች ውጭ አይቼው አላውቅም። ኳስ ተጫዋች ባልሆን ኖሮ ብዬ አስቤ ሰለማላውቅ ፈጣሪ ይመስገን ህልሜን እየኖርኩ ነው ።
ሀትሪክ :- ዛሬ አመሻሽ 12:00 ጀምሮ ከሊጉ መሪ መቻል ተጠባቂ ጨዋታ ታደርጋላችሁ። ካሸነፋችሁ የሊጉን መሪ ትሆናላችሁ። ለጨዋታው ያደረጃችሁት ዝግጅት ምን ይመስላል ? የተለየ ዝግጅት አድርጋችኋል ?
ብሩክ ማርቆስ :- ለዛሬው ጨዋታ ብለን የተለየ የምንለው ዝግጅት አላደረግንም ። ለሁሉም ክለቦችና ለሁሉም ጨዋታዎች ተመሳሳይ የሆነ ዝግጅት ነው የምናደርገው ።
ሀትሪክ :- በጨዋታው አሸንፋችሁ ወደ መሪነት ለመምጣት ያለው የቡድኑ መንፈስ ምን ይመስላል ?
ብሩክ ማርቆስ :- ቡድናችን ጥሩ መነቃቃት ላይ ነው ያለው ። 90 ደቂቃውን ለመፋለም ዝግጁ ነን።
ሀትሪክ :- ምስጋና
ብሩክ ማርቆስ :- በመጀመሪያ ዕድሜና ጤና ሰጥቶ ለዚህ ያደረሰኝ ፈጣሪ ይመስገን ። በመቀጠል ከልጅነቴ ጀምሮ ከእኔና ከእኔ ህልም ጋር የቆሙትን ቤተሰቦቼን ከልብ አመሰግናለሁ ። ስቀጥል ለመጀመሪያ ጊዜ ወደ ሀዲያ ሆሳዕና እንድገባ አምኖኝ ከዛም በአጭር ጊዜ ውስጥ ወደ ሜዳ እንድገባ እድሉን የሰጠኝን አሰልጣኝ ያሬድ ገመቹን ከልብ አመሰግናለሁ ፤ በየቀኑ እንድሻሻል የሚያግዘኝ አሰልጣኝ ግርማ ታደሰ(መንቾ) እና የአሰልጣኝ ቡድን አባላት ፣ አጠቃላይ የቡድን ጓደኞቼን ፣ የሀዲያ ሆሳዕና እግር ኳስ ክለብ ፅ/ቤት እና የክለቡ ስራ አመራር ቦርድ እንዲሁም የሀዲያ ሆሳዕና ደጋፊዎችን ሁሌም ከጎኔ ሰለሆናችሁ ከልብ አመሰግናለሁ ።
ሀትሪክ ስፖርት ድህረገፅም እንግዳችሁ ስላደረጋቹኝ ከልብ አመሰግናለሁ ።


