በርካታ ውዝግቦችን በሜዳ ላይ እና ከሜዳ ውጪ በታየበት የ ቤት ኪንግ ኢትዮጵያ ፕርሚየር ሊግ ደጋፊዎች ከስታዲየም መግቢያ ጋር ቅሬታቸውን ሲያሰሙ ሲስተዋል በስታዲየም የሚገቡ ደጋፊዎች ተገቢውን ወቅታዊ ጥንቃቄ ሳያደርጉ ተስተውሎ አልፏል ።
የ ቤት ኪንግ ኢትዮጵያ ፕርሚየር ሊግ ሁለተኛ ሳምንት ላይ ሲደርስ የተለያዩ ሁነቶችን አሳይቶ አልፏል ። ኢትዮጵያ ቡና ፣ ቅዱስ ጊዮርጊስ ፣ ሰበታ ከተማ እንዲሁም ወላይታ ድቻ የመጀመሪያ ድላቸውን ሲያስመዘግቡ በተቃራኒው ሀድያ ሆሳዕና ተከታታይ ድል ማስመዝገብ ችለዋል ።
- ማሰታውቂያ -
በኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን የሚተዋወቁትን ኢንስትራክተር አብርሀም መብርሀቱ እና ሙሉጌታ ምህርት በዚህ ሳምንት በተቃራኒው ሲገናኙ የአሰልጣኝ አብርሀም መብርሐቱ ሰበታ ከተማ የበላይነቱን ወስዶ የመጀመሪያ ሶስት ነጥባቸውን ማሳካት ችለዋል ።
በሳምንቱ ታላቅ ጨዋታ ኢትዮጵያ ቡና በጎዶሎ ተጫዋች ተጫውተው ፋሲል ከነማን በማሸነፍ የውድድር ዓመቱን የመጀመሪያ ድላቸውን ማስመዝገብ ችለዋል ። ረብጣ ገንዘቦችን በማውጣት ተጫዋቾችን ያስፈረሙት ፈረሰኞቹ በሁለተኛው ሳምንት ፍሬ አፍርቶላቸው በከንዓን ማርክነህ እና አዲስ ግደይ ግቦች ታግዘው ወሳኝ ሶስት ነጥብ ይዘው ለመውጣት ችለዋል ።
በዘንድሮው የውድድር ዓመት ጠንካራ ተፎካካሪ ይሆናሉ ተብሎ የሚታመኑት ባህር ዳር ከተማ እና ሀድያ ሆሳዕናዎች ሲገናኙ ዳዋ ሆቴሳ በጭማሪ ደቂቃ ባስቆጠራት ግብ ያለመሸነፍ ጉዟቸውን አስቀጥለዋል ።
በሁለተኛው ሳምንት የ ቤት ኪንግ ኢትዮጵያ ፕርሚየር ሊግ አስራ አምስት ግቦች ሲቆጠሩ ከመጀመሪያው ሳምንት በሁለት ያነሰ ሆኖ አልፏል ። በዚህ ሳምንት ሶስት ተጫዋቾች ተመስገን ካስትሮ ፣ አናጋው ባድግ እና ዳዋ ሆቴሳ የቀይ ካርድ ሲመለከቱ ካለፈው ሳምንት ከፍ ብሎ ታይቷል ።የወላይታ ድቻው ስንታየሁ መንግስቱ በሳምንቱ ሁለት ጎሎችን ማስቆጠር የቻለ ብቸኛው ተጫዋች ሆኖ ሲያልፍ በዚህ ሳምንት ከተቆጠሩ አስራ አምስት ጎሎች መካከል አስራ ሁለቱን አዳዲስ ተጫዋቾች ሲያስቆጥሩ አቡበከር ናስር እና ዳዋ ሆቴሳ ብቸኞቹ በተከታታይ ጨዋታዎች ግብ ያስቆጠሩ ተጫዋቾች ሆነው አልፈዋል ።
በዚህ ሳምንት ከተቆጠሩ አስራ አምስት ጎሎች ውስጥ አምስቱ በመጀመሪያው አጋማሽ ሲቆጠሩ ካለፈው ሳምንት ጋር ተመሳሳይነት ያለው ሆኖ አልፏል ። ሁለተኛ ሳምንት ላይ በደረሰው የ ቤት ኪንግ ኢትዮጵያ ፕርሚየር ሊግ በድምሩ ሰላሳ ሁለት ጎሎች ከመረብ ሲያርፉ ሀያ ሁለቱ በሁለኛው አጋማሽ መቆጠር ችለዋል ።
የሀድያ ሆሳዕናው መሀመድ ሙንታሪ ፣ የወላይታ ድቻው ሰዒድ ሀብታሙ ፣ የወልቂጤ ከተማው ጀማል ጣሰው እንዲሁም የጅማ አባ ጅፋሩ ጃኮ ፔንዞ መረባቸውን በሁለተኛው ሳምንት ያላስደፈሩ ግብ ጠባቂዎች ናቸው ። በዚህ ሳምንት እንደ መጀመሪያው ሳምንት ሁሉ አራት የፍፁም ቅጣት ምት ሲሰጥ አራቱም ወደ ግብነት ለመቀየር ችለዋል።
በሁለተኛው ሳምንት የ ቤት ኪንግ ኢትዮጵያ ጨዋታዎች ላይ አስራ አራት የውጭ ሀገር ተጫዋቾች በቋሚ አሰላለፍ ላይ ሲጀምሩ አንዳቸውም ግብ ማስቆጠር ሳይችሉ ለተከታታይ ሁለተኛ ሳምንት ለመዝለቅ ችለናል ። በቋሚነት ከ ኢትዮጵያ ቡና እና ወላይታ ድቻ በተጨማሪም ሰበታ ከተማ ፣ ወልቂጤ ከተማ እንዲሁም አዳማ ከተማ በዚህ ሳምንት ምንም የውጭ ሀገር ተጫዋቾችን ያልተጠቀሙ ክለቦች ናቸው ።
የሶስተኛ ሳምንት የ ቤት ኪንግ ኢትዮጵያ ፕርሚየር ሊግ ከነገ በስቲያ ዕሮብ ጀምሮ መካሄዳቸውን ሲቀጥሉ በዚህ ሳምንት ሰበታ ከተማ አራፊው ቡድን ሲሆን የተመረጡ ጨዋታዎች ብቻ በ ሱፐርስፖርት የሚተላለፍ ይሆናል ።