በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ሀድያ ሆሳዕናና ኢትዮጵያ ቡና ባደረጉት ጨዋታ ላይ በአቡበከር ናስርና በአርቢትሩ ሚካኤል ጠዓመ መሃል የተነሳው አለመግባባት ለአርቢትሩ ከውድድሩ ስፍራ መመለስ ምክንያት ሆነ።
በጨዋታው ሀድያ ሆሳዕና የገባ ግብ ተሽሮበትም ፍጹም ቅጣት ምት ተከልክሎም 1ለ0 የረታ ሲሆን በጨዋታው መሃል አለመግባባት ውስጥ የገባው አቡበከር አፉን ሸፍኖ ዳኛውን ሲናገር ዳኛውም እየዞረ ምላሽ ሲሰጥ ታይቷል።
ጨዋታው እንዳለቀ የኢትዮጵያ ቡናው አሰልጣኝ ካሳዬ አራጌ “የመሃል ዳኛው አቡበከርን አስጸያፊ ቃል ሲናገረው ሰምቻለሁ” ማለቱን ተከትሎ ውስጥ ውስጡን ሲብሰለሰል የነበረው ጉዳይ ፈንድቷል። አሰልጣኙ ከጨዋታው በኋላ አርቢትሩን ለማናገር የሞከረ ሲሆን ” “ለሚዲያ ከመግለጽህ በፊት አቡበከር ምን እንዳለኝ የቡድን አጋሩ አማኑኤልን ጠይቀህ አውራኝ አሁን ላናግርህ አልፈልግም” በማለት አርቢትሩ ለካሳዬ መመለሱም ተሰምቷል። ዳኛው ጨዋታው ካለቀ በኋላ እንደሰደበው ሪፖርት ሊጽፍ ሲል የብሄራዊ ዳኞች ኮሚቴ አባሉና የጨዋታው ኮሚሽነር ግዛቴ ዓለሙ መጻፍ እንደሌለበት ሜዳ ውስጥ በቀይ ካርድ ሳያስወጣው አሁን መጻፉ ልክ አይደለም ብለውት ሳይጽፍ መቅረቱ ታውቋል።
አርቢትሩ ለብሄራዊ ዳኞች ኮሚቴ በሰጠው የእምነት ቃል “አቡበከር ውሳኔዎቹን በመቃወም እናቴን በመስደቡና በመዛለፉ ተበሳጭቼ እኔም ተመሳሳይ ስድብ ሰድቤዋለሁ” በማለት ቃሉን ሰጥቷል። ኢትዮጵያ ቡናም ከጨዋታው በኋላ ዳኛው አቡበከር ላይ አስጸያፊ ቃል መጠቀሙን በመግለጽ የክስ ደብዳቤ በማስገባቱ ኮሚቴው በካርድ መጠቀም አሊያም ሪፖርት ማድረግ እንደነበረበት በመግለጽ ለስህተቱ ወደመጣበት እንዲመለስ ወስኗል። አርቢትሩ በካርዱ ወይም በሪፖርቱ ክስተቱን ባለመግለጹ የኢትዮጵያ ቡናው ወሳኝ አጥቂ አቡበከር ናስር ግን ከቅጣት አምልጧል።
ዳኛውና ኮሚሽነሩ በህጉ መመረት የተፈጠረውን መግለጽ ቢኖርባቸውም ያንን ባለማድረጋቸው ህጉን ጥሰዋል። ኮሚቴው አርቢትሩ እንዲመለስ ቢወስንም ሪፖርቱን አትጻፍ ያሉት የኮሚቴው አባል የሆኑት አቶ ግዛቴ ላይ የተወሰደ ርምጃ ግን የለም በቀጣይ የሊግ ኩባንያው የውድድርና ስነስርዓት ኮሚቴ ርምጃ ግን የሚጠበቅ ይሆናል።
አሁንም እንደተለመደው ውሳኔው ላይ የለንበትም አልሰማንም የሚሉ የብሄራዊ ዳኞች ኮሚቴ አባላት የተከሰቱ ሲሆን ኮሚቴው መቼ ተመሳሳይ ቋንቋ ይናገራል የሚለውም የሚያጓጓ ሆኗል።
አስተያየት ይስጡ