በውጤት እጦት ውስጥ የሚገኘው አርባምንጭ ከተማ አዲስ አሰልጣኝ ሊሾም ነው።
በፕሪምየር ሊጉ ላይ እጅግ ደካማ የውድድር ጉዞን እያደረገ የሚገኘው አርባምንጭ ከተማ በያዝነው የውድድር ዘመን ከታችኛው የሊግ ዕርከን በማሳደግ ሲያሰለጥን ከነበረው አሰልጣኝ በረከት ደሙ ጋር ከተለያየ በኋላ በጊዜያዊ አሰልጣኝነት የቀድሞው ተጫዋቹ አበባው ቡጣቆን በቦታው ቢሾምም አሁንም ከወጣበት ቅርቃር መላቀቅ አልቻለም። አንድም ጨዋታ ማሸነፍ ሳይችል በስምንቱ ተሸንፎ ፣ ስምንት አቻ ከወጣባቸው ጨዋታዎች በሰበሰባቸው 8 ነጥቦች በወራጅ ቦታ ሀያኛው ላይ የተቀመጠው ክለቡ ቀጣዩ የአመቱ ሦስተኛው አሰልጣኙ የኤ ላይሰንስ ባለቤቱ አዲሴ ካሳን ለማድረግ መቃረቡን ያገኘውት መረጃ ያመላክታል።
ከ1993 ጀምሮ የሀዋሳ ከተማ ረዳት አሰልጣኝ በመሆን ወደ ስልጠናው አለም በመግባት ከዛም በደቡብ ፖሊስ እና ወልቂጤ ከተማ በኋላ 2011 ላይ በድጋሚ ወደ ሀዋሳ ከተማ በመመለስ ክለቡን በዋና አሰልጣኝነት መምራት የቻሉ ሲሆን ከከፍተኛ ሊጎቹ ካፋ ቡና እና ቡታጅራ ከተማ ቀጥሎ ደግሞ ሲዳማ ቡናን በረዳት እና በዋና አሰልጣኝነት ጭምር መምራታቸው የሚታወስ ሲሆን ቀጣዩ መዳረሻው ደግሞ አዞዎቹ ቤት ሊሆን መቃረባቸውን በሰበሰብኳቸው መረጃዎች አረጋግጫለሁ።


