“እንዳሰብኩት ለሃገሬ ኮት ዲቯር ኩራት የሆነው የኤቢምፔ ኦሊምፒክ ስታዲየም የምረቃ በዓል ላይ በጊዜ መድረስ ባለመቻሌ እጅግ በጣም አዝኛለው፡፡ የኤቢምፔ ኦሊምፒክ ስታዲየም ለአፍሪካና ለኮት ዲቯር ስፖርት ትልቅ ጌጥ ነው በዝግጅቱ ለምትሳተፉ ሁሉ መልካም የምረቃ በዓል ይሁንላችሁ::”ሲል መልዕክቱን ያስተላለፈው የቀድሞው የቼልሲና ተጫዋች ዲዲዬ ድሮግባ ነው፡፡
የኤቢምፔ ኦሊምፒክ ስታዲየም ዛሬ የሃገሪቱ ፕሬዚዳንት አላሳን ዋታራ በተገኙበት በታላቅ ድምቀት ተመርቋል፡፡ ጥቅምት 2016 ተጀምሮ ከአራት ዓመታት ሥራ በኋላ ዛሬ ምረቃውን ያደረገው ይሄ ግዙፍ ስታዲየም በቻይናና በኮት ዲቯር መንግስታት ትብብር የተሰራ ነው፡፡ ስታዲየሙ ተጀምሮ እስከሚጠናቀቅ ድረስ 143 ቢሊዮን የምዕራብ አፍሪካ ፍራንክ የፈጀ ሲሆን 60012 ሰዎችን የማስተናገድ አቅም እንዳለው ተጠቅሷል፡፡
“ይህን በሥነ-ህንጻ ውበቱ የአፍሪካ ጌጥ የሆነ፣ በቻይናና በኮት ዲቯር መንግስታት ትብብር የተሰራ ታላቅ ስታዲየም ከፊታችሁ ሆኜ ስመርቅ የሚሰማኝን ደስታ ቃላት ሊገልጹልኝ አይችሉም”ብለዋል፡፡
ይህ ስታዲየም በትልቅነቱ የካሜሮኑን ኦሊምቤ ስታዲየምና የዳካሩን ሊኦፖል ሴዳር ሴንጎር ስታዲየምን ተከትሎ ከአፍሪካ አስረኛ ደረጃ ላይ የተቀመጠ ስታዲየም ሲሆን በመጪው መጋቢት ወር ኮት ዲቯር የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድንን የምታስተናግድበት ስታዲየም እንደሚሆን ይጠበቃል፡፡