አሰልጣኝ ፋሲል ተካልኝን በዋና አሰልጣኝነት ከሾሙ በኋላ በዝዉዉር ገበያው ላይ በንቃት እየተሳተፉ የሚገኙት አዳማ ከተማዎች በዛሬዉ ዕለት ደግሞ የሶስት ተጫዋቾችን ዝዉዉር ማጠናቀቃቸው ተረጋግጧል።
የመጀመሪያው ፈራሚ ከሀላባ ከተማ የተገኘዉ የመስመር አጥቂው ዮናስ ገረመው ሲሆን ዘንድሮ መቐለ 70 እንደርታ በሊጉ አለመሳተፉን ተከትሎ እስከ ዓመቱ አጋማሽ ሳይጫወት ከቆየ በኃላ በመጋቢት ወር ወደ ሲዳማ ቡና አምርቶ ከቀድሞው አሰልጣኙ ገብረመድህን ሀይሌ ጋር የግማሽ ዓመት ቆይታን ካደረገ በኃላ በሁለት አመት ውል ለአዳማ ፊርማዉን ማኖሩ ታዉቋል፡፡
ሌላኛዉ የክለቡ ፈራሚ ደግሞ ተከላካዩ አዲስ ተስፋዬ ሲሆን የድሞዉ የወላይታ ድቻ እና መከላከያ ተጫዋች ያለፉትን ሁለት አመታት በሰበታ ከተማ ቤት ቆይታ ካደረገ በኋላ ለአዳማ ፊርማውን አኑሯል።
በዛሬው ዕለት ሶስተኛ ፈራሚ በመሆን አዳማ ከተማን የተቀላቀለዉ ደግሞ የአማካይ ስፍራ ተጫዋቹ ታደለ መንገሻ መሆኑ ታዉቋል። ረዘም ላለ አመታት ከተጫወተበት ቅዱስ ጊዮርጊስ በመዉጣት ያለፉትን ሁለት አመታት በሰበታ ከተማ ቤት መጫዎት የቻለዉ ታደለ አሁን ደግሞ በቅዱስ ጊዮርጊስ ቤት ሲያሰለጥነዉ የነበረዉን አሰልጣኝ ፋሲል ተካልኝ በመከተል አዳማ ከተማ ለመጫዎት ፊርማዉን አኑሯል።
- ማሰታውቂያ -
ዘንድሮ ከሊጉ ወርዶ የነበረዉ አዳማ ከተማ የትግራይ ክልል ክለቦች በሊጉ አለመሳተፋቸዉን ተከትሎ በሀዋሳ ዩኒቨርስቲ በተደረገዉ ዉድድር ላይ የአንደኝነት ደረጃን በመያዝ ዳግም በሊጉ የሚያሳትፈዉን እድል ማግኘቱ ይታወሳል።


