በኢትዮጵያ ኘሪሚየር ሊግ 22ኛ ሳምንት የውድድር መርሀ ግብር ድሬዳዋ ከነማ እና ኢትዮጵያ ቡና መጋቢት 07/2009 ዓ.ም ጨዋታቸውን ባካሄዱበት ወቅት ከተከሰተው የስፖርታዊ ጨዋነት ጋር ተያይዞ ድሬዳዋ ከነማ አንድ ጨዋታ በዝግ ስታዲየም እንዲጫወት ተወስኖበታል፡፡ በኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን የዲስኘሊን ኮሚቴ የዕለቱን ጨዋታ የመሩት ዳኞችና ኮሚሽነሮች ያቀረቡትን ሪፖርት መርምሮ ባሳለፈው ውሳኔ የድሬዳዋ ከነማ እግር ኳስ ደጋፊዎች በኢትዮጵያ ቡና ተጫዋች ጋቶች ፓኖም ላይ ፀያፍና በስፖርት ማዘውተሪያ ስፍራዎች በእጅጉ የተወገዘ ድርጊት መፈፀማቸው ተረጋግጧል፡፡ በእዚሁ መሰረት የድሬዳዋ ከነማ እግር ኳስ ክለብ 75,000 ብር/ሰባ አምስት ሺህ ብር/ የገንዘብ ቅጣትና ቀጣዩን የኘሪሚየር ሊግ ጨዋታ ያለደጋፊ እንዲጫወት ተወስኖበታል፡፡
በተመሳሳይ በዕለቱ በሁለት ቢጫ ካርድ ከሜዳ የወጣው የኢትዮጵያ ቡናው ጋቶች ፓኖም በፈፀመው ጥፋት የድሬዳዋ ከነማ ደጋፊዎች የፈጠሩበትን የስነልቦና ጫና ከግምት ውስጥ በማስገባት የአንድ ጨዋታ ቅጣት ተላልፎበታል፡፡ የድሬዳዋ ከነማው የህክምና ባለሙያ አስራት ለገሠ ደግሞ በእለቱ ለፀብ የሚያነሳሳ ድርጊት በመፈፀሙ ምክንያት አራት ጨዋታዎች እንዲታገድና ብር 5,000/አምስት ሺህ ብር/ እንዲቀጣ ተወስኖበታል፡፡
- ማሰታውቂያ -
የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን
ምንጭ: የኢእፌ