ከኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ መጀመር በፊት ክለቦች እንደ አቋም መለኪያ የሚጠቀሙበት የአዲስ አበባ ከተማ ዋንጫ በአዲስ አበባ እግር ኳስ ፌደሬሽን አዘጋጅነት ለ13ኛ ጊዜ ከ ጥቅምት 3-18 2011 ድረስ እንደሚካሄድ ከአዲስ አበባ እግር ኳስ ፌደሬሽን ያገኘነው መረጃ ያስረዳል።
በዚህ ውድድር ላይም 8 ክለቦች የሚሳተፉ ሲሆን እስካሁን 7 ቡድኖች ታውቀዋል። እነሱም በ2011 የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የሚሳተፉት ሶስቱ የአዲስአበባ ክለቦች ማለትም የአምናው የውድድሩ አሸናፊ ቅ/ጊዮርጊስ የአምናው የውድድሩ የዋንጫ ተፋላሚ ኢትዮጵያ ቡና እና መከላከያ ሲሆኑ በተጋባዥነት ደግሞ አምና ተጋባዥ የነበሩት አዳማ ከተማና ጅማ አባጅፋር እንዲሁም ዘንድሮ የተጋበዙት ፋሲል ከተማ እና ወላይታ ድቻ ይገኙበታል። ስምንተኛው ቡድን ከኢትዮጵያ ውጪ ከምስራቅ አፍሪካ ከሚገኝ ክለብ አንዱን ለመጋበዝ ጥረት እየተደረገ እንደሆነ እና እሱ የማይሳካ ከሆነ አምና ከፕሪሚየር ሊጉ የወረደው ከኢትዮ-ኤሌክትሪክ እና አዲስአበባ ከተማ አንዱ ሊሆን እንደሚችል ተጠቅሷል።
ሆኖም ግን ውድድሩ እንዲካሄድ የተያዘለት ቀነ ቀጠሮ የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ይጀመራል ተብሎ ከታሰበበት ቀን ጥቅምት 17/2011 ጋር የሚጋጭ ሆኗል። ይህንንም ተከትሎ የአዲስአበባ እግርኳስ ፌደሬሽን እና የኢትዮጵያ እግርኳስ ፌዴሬሽን ሰኞ መስከረም 7/2011 ዓ.ም ውይይት እንደሚያደርጉ ተሰምቷል።
አስተያየት ይስጡ