በአዲስ አበባ እየተገነባ ያለው የብሄራዊ ስታዲየም ሁለተኛው ምዕራፍ ሥራ በቅርቡ ይጀመራል
በኢትዮጵያ ግዙፍ የተባለውና በአዲስ አበባ እየተገነባ ያለው ብሄራዊ ስታዲየም ሁለተኛ ምእራፍ ሥራ በቅርቡ ይጀምራል ተባለ።
የዛሬ አራት ዓመት የተጀመረው የመጀመሪያው ምእራፍ ግንባታ ተጠናቋል።
በአዲስ አበባ ቦሌ አካባቢ በቻይናው ስቴት ኮንስትራክሽን ኢንጂኒየሪንግ ኩባንያ እየተገነባ ያለው ስታዲየም 62 ሺህ ስዎችን የመያዝ አቅም ያለው አለው።
ከስታዲየሙ ሜዳ ሳር ማልበስና የመሮጫ ትራክ በስተቀር በአሁኑ ወቅት የመጀመሪያው ምእራፍ ሥራ የተጠናቀቀ ሲሆን ይህም አጠቃላይ የህንፃውን መዋቅር ጨምሮ የስፖርተኞች ማረፊያ፣ ቢሮዎች፣ የጋዜጠኞች ማስተናገጃ ወዘተ ያካትታል።

የመጀመሪያው ምእራፍ የፕሮጀክቱ ሥራ በተወሰነ ጊዜ የዘገየ ሲሆን ለዚህም ምክንያቶቹ ከውጭ የሚገቡ እቃዎች በጊዜው አለመድረስና የውጭ ምንዛሬ እጥረት ተጠቅሰዋል።
በቅርቡ ይጀምራል ተብሎ በሚጠበቀው ሁለተኛው ምእራፍ የስታዲየሙ ፕሮጀክት ከሚካተቱት ሥራዎች መካከል የመጫወቻ ሜዳውን ሳር ማልበስ፣ የመሮጫ ትራክ ማንጠፍ፣ የስታዲየሙን ጣሪያ ማልበስና ወንበር መግጠም ይገኙበታል።
ከዚህም ሌላ ሰው ሰራሽ ሀይቅ፣ የሄሊኮፍተር ማረፊያ፣ ዘመናዊ የደህንነት ካሜራ ሌሎች በርካታ ስራዎች ይከናወናሉ ተብሏል።
ሁለተኛውም ምእራፍ ሥራ ለማጠናቀቅ በጠቅላላው 900 ያህል ቀናት እንደሚፈለግ የፌዴራል ስፖርት ኮሚሽን አስታውቋል።
ኮሚሽነሩ አቶ ኤልያስ ሽኩር እንዳሉት ለመጀመሪያው ምዕራፍ ግንባታ ከ2. 47 ቢሊዮን ብር በላይ ወጪ ተደርጋል።
ሁለተኛው ምእራፍ የግንባታ ሥራ ከዚህ የበለጠ ወጪ ይጠይቃል ብለዋል።

ለሁለተኛው ምእራፍ ሥራ የኮንትራክተር ጨረታ ወጥቶ አሸናፊው የተለየ ሲሆን በቅርቡ የኮንትራት ውሉ እንደተጠናቀቀ ሥራው ይጀመራል ሲሉም ኮሚሽነሩ አስታውቀዋል።
ስታዲየሙ ተጠናቆ ለአገልግሎት ሲበቃ ዓለም አቀፍ የእግር ኳስ ውድድሮችን ከማስተናገድ በተጨማሪ ሌሎች እንደ አትሌቲክስ አይነት ውድድሮችን ለማስተናገድ ምቹ አጋጣሚን የሚፈጥር ነው።
አስተያየት ይስጡ