በአፍሪካ ኮንፌዴሬሽን ዋንጫ ምድብ ድልድል ለመግባት የመልስ ጨዋታውን ለማድረግ ወደ ጎንጎ ብራዛቢል ያቀናው የኢትዮጵያው ቅዱስ ጊዬርጊስ በካራ ብራዛቢል በመለያ ምት 5ለ3 ተሸንፎ ከውድድሩ ውጭ ሁኗል፡፡
ቅዱስ ጊዬርጊሶች የጎንጎውን ካራ ብራዛቢል በመጀመሪያው አዲስ አበባ ስታዲዬም በሜዳቸው ባስተናገዱበት ጨዋታ በ78ኛው ደቂቃ አዳነ ግርማ ባስቆጠራት ብቸኛ ግብ 1-0 ማሸነፋቸው የሚታወስ ቢሆንም ሁለቱ ክለቦች ዛሬ ብራዛቪል ላይ ባደረጉት የመልስ ጨዋታ ባለሜዳዎቹ ካራዎች በአጥቂያቸው ንጎማ ምቦ የ34ኛ ደቂቃ ጎል ፈረሰኞቹን ሲያሸንፉ የጨዋታው ድምር ውጤት 1-1 ሆኖ ነበር፡
በመሆኑም ወደ ምድብ ድልድል አላፊውን ክለብ ለመለየት በተሰጡት መለያ ምቶች ባለሜዳዎቹ የተሰጧቸውን 5ቱንም ምቶች ወደ ጎል ሲቀይሯቸው ፈረሰኞቹ ከአምስቱ ምቶች 3 አስቆጥረው 2ቱን ወደ ግብ መቀየር ሳይችሉ በመለያ ምት 5-3 ተሸንፈው ከአፍሪካ ኮንፌደሬሽን ዋንጫ ውድድር ውጭ ሁነዋል፡፡
በዘንድሮው የአፍሪካ መድረክ ኢትዮጵያን በመወከል ብዙ ርቀት ለመጓዝ ዕቅድ የነበራቸው ፈረሰኞቹ በሁለቱም የአፍሪካ መድረክ ውድድሮች ሳይሳካላቸው ከውድድሩ በጊዜ ተሰናብተዋል፡፡
ፈረሰኞቹ ኢትዮጵያ ወክለው በአፍሪካ ኮንፌደሬሽን ዋንጫ የመሳተፍ ዕድሉን ያገኙት መጀመሪያ ይሳተፉበት ከነበረው የአፍሪካ ቻምፒየንስ ሊግ ውድድር ወደ ምድብ ድልድል ሳይገቡ በዩጋንዳው ኬሲሲኤ በደርሶ መልስ ድምር ውጤት 1-0 ተሸንፈው በመውጣታቸው ነበር፡፡
አስተያየት ይስጡ