በ17ኛው ሳምንት የፕሪሚየር ሊጉ መርሃ ግብር መጋቢት 20 ቀን 2010 ዓ.ም በአዲግራት ስታዲየም ሁለቱ ቡድኖች ባደረጉት ጨዋታ የመጀመሪያው አጋማሽ በወልዋሎ አዲግራት መሪነት 1-0 እንደተጠናቀቀ በተፈጠረው የደጋፊዎች ረብሻ ምክንያት ጨዋታው መቋረጡ ይታወሳል።
የመጀመሪያ አጋማሽ ተጠናቆ ሁለቱ ቡድኖች ወደ መልበሻ ክፍል ከገቡ በኋላ የተፈጠረው ረብሻ ለረጅም ጊዜ በመቆየቱ ምክንያት የጨዋታው አመራሮች የሁለተኛው አጋማሽ ጨዋታ እንዳይካሄድ ወስነው ጨዋታው ተቋርጧል።

የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌደሬሽን የዲስፕሊን ኮሚቴ በወልዋሎ አዲግራት ዩንቨርስቲ ላይ የ70 ሺህ ብር እንዲሁም በመቐለ ከተማ ላይ የ90 ሺህ ብር ቅጣት አስተላልፏል።
ሁለቱ ቡድኖች ቅጣቱ የተላለፈባቸው የየክለቦቹ ደጋፊዎች ቁሳቁስ በመወራወር የረብሻ ምክንያት በመሆናቸውና ጨዋታው እንዲቋረጥ በማድረጋቸው እንደሆነም ፌዴሬሽኑ ገልጽዋል።
የተቋረጠው ጨዋታ ከአዲግራት ከተማ 165 ኪሎ ሜትር ርቆ በሚገኝ በፌደሬሽኑ የተመዘገበ ሜዳ እንዲካሄድና ይህንንም የሊግ ኮሚቴው እንዲያስፈጽም መወሰኑን ሲታወቅ፣
የቅጣት ውሳኔው ለሁለቱ ክለቦች በደብዳቤ እንዲደርሳቸው መደረጉንና ጨዋታው የሚካሄድበት ቦታና ቀን በቀጣይ ጊዜ ይፋ እንደሚደረግ ፌዴሬሽኑ አስታውቋል ።
አስተያየት ይስጡ