የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 4ኛ ሳምንት 7ጨዋታዎች ነገ ይደረጋሉ።
የ2012 የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 4ኛ ሳምንት 8 ጨዋታዎች በሳምንቱ መጨረሻ የሚደረጉ ሲሆን 7ጨዋታዎች ነገ (ቅዳሜ) እንዲሁም 1ጨዋታ ደግሞ ከነገ በስትያ (እሁድ) የሚደረግ ይሆናል። ከነዚህ መካከል 6ቱ ጨዋታዎች ክልል ላይ ሲደረጉ ሁለቱ ደግሞ አዲስ አበባ ላይ ይደረጋሉ።
ቅዳሜ ከሚደረጉት ጨዋታዎች መካከል አዳማ ላይ አዳማ ከተማ ከወላይታ ድቻ የሚያደርጉት ጨዋታ ይጠበቃል። ባለሜዳው አዳማ ከተማ በዘንድሮው የሊጉ ውድድር ከቅ/ጊዮርጊስ በመቀጠል በሊጉ ግብ ያልተቆጠረበት ሌላው ክለብ መሆን የቻለ ሲሆን በሊጉ 1ጊዜ አሸንፎ በሁለቱ ጨዋታዎች ያለግብ አቻ ተለያይቷል። በ3ኛው ሳምንት አዳማ ከተማ ወደ ሰበታ አቅንቶ ከሰበታ ከተማ ጋር ያለ ግብ አቻ ተለያይቶ ሲመለስ ወላይታ ድቻ ደግሞ በሜዳው ቅ/ጊዮርጊስን በሜዳ አስተናግዶ እንደ አዳማ ከተማ ሁሉ ያለግብ አቻ መለያየቱ ይታወሳል። ሁለቱ ክለቦች በደረጃ ሰንጠረዡ በአንድ ነጥብ ተበላልጠው አዳማ ከተማ በ5 ነጥቦች 5ኛ ደረጃ ላይ ሲቀመጥ ወላይታ ድቻ ደግሞ በ4ነጥቦች 7ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ፌደራል አርቢትር ዳንኤል ግርማይ የሚመራው ይህ ጨዋታ 9:00 ሲል የሚጀምር ይሆናል።
በሌላ የሊጉ የ9 ሰዓት ጨዋታ ፋሲል ከተማን ከአዲስ አዳጊው ሀድያ ሆሳዕና ጋር የሚያገናኘው ጨዋታ በጉጉት ይጠበቃል። በፌደራል አርቢትር ተፈሪ አለባቸው የሚመራው ይህ ጨዋታ ለሁለቱም ቡድኖች በጣም ወሳኝ ነው። ፋሲል ከነማ ከመሪዎቹ ቡድኖች ላለመራቅ ሀድያ ሆሳዕና ደግሞ የሊጉን የመጀመሪያ ነጥብ አስመዝግቦ ከወራጅ ቀጠናው ለመውጣት የሚያደርጉት ጨዋታ በመሆኑ በእግር ኳስ ተመልካቹ ዘንድ በጉጉት እንዲጠበቅ አድርጎታል። ፋሲል ከነማ በ2ኛው ሳምንት በሜዳው ድሬዳዋ ከተማ ላይ 5ግቦችን አዝንቦ ማሸነፍ ቢችልም በ3ኛው ሳምንት ግን ወደ ወልቂጤ ተጉዞ በወልቂጤ ከተማ አስደንጋጭ የ 1-0 ሽንፈት አጋጥሞት ተመልሷል። እስካሁን በሊጉ ድል ሊቀናው ያልቻለው አዲስ አዳጊው ሀድያ ሆሳዕና በ3ኛው ሳምንት ጨዋታ ወደ ድሬ ተጉዞ በድሬዳዋ ከተማ የ1-0 ሽንፈት አስተናግዷል። ሁለቱ ቡድኖች ባደረጓቸው ሶስት ጨዋታዎች ሀድያ ሆሳዕና ሰበታ ከተማን በግብ ክፍያ በመብለጥ በ1ነጥብ 15ኛ ደረጃ ላይ ሲገኝ ፋሲል ከተማ ደግሞ በ4ነጥቦች 6ኛ ደረጃ ላይ መቀመጥ ችሏል።
አስተያየት ይስጡ