ቅዱስ ጊዮርጊስ ከ ስሁል ሽረ
ዋና ዳኛ፡ ኢንተርናሽናል አርቢትር ለሚ ንጉሴ
በሜዳና ከሜዳ ውጪ መረጋጋት የተሳነው ስሁል ሽረና ተከታታይ የሆነ አቋም ማሳየት ያቃተው ቅዱስ ጊዮርጊስን የሚያገናኘው ይህ ጨዋታ ቅዳሜ 10 ሰዓት በአዲስ አበባ ስታድየም ይደረጋል። ፈረሰኞቹ ወሳኝ ተጨዋቾቻቸው የሆኑት አስቻለው ታመነ፣ሳላሀዲን ሰይድ እንዲሁም ፓትሪክ ማታሲ አሁንም በጉዳት የሚያጡ ሲሆን፤ በጉዳት ከሜዳ ርቀው የነበሩት ጌታነህ ከበደ፣ ሳላሃዲን በርጌቾ እና አሜ መሀመድ ከጉዳታቸው አገግመው ወደ ሜዳ ተመልሰዋል።
ስሁል ሽረዎች በበኩላቸው አራት ወሳኝ ተጨዋቾቻቸው ሳሊፍ ፎፎና፣ ዲድዬ ሌብሪ፣ ያሰር ሙገርዋና አክሊሉ ዋለልኝ በደሞዝ አለመከፈል ምክንያት ለነገው ጨዋታ የማያሰልፋ ሲሆን ግብ ጠባቂያቸውን ምንተስኖት አሎን በጉዳት የሚያጡ ይሆናል።
ሲዳማ ቡና ከ መቐለ 70 እንደርታ
ዋና ዳኛ ፡ ፌደራል አርቢትር አሸብር ሰቦቃ
- ማሰታውቂያ -
ሁለት ተከታታይ ጨዋታዎችን በማሸነፍ ጥሩ ወቅታዊ አቋም ላይ የሚገኙት ሲዳማ ቡና ና የወቅቱ ሻምፒዮን መቐለ 70 እንደርታን የሚያገናኘው ይህ ጨዋታ ጠንካራ ፋክክር ሊታይበት እንደሚችል ይገመታል።
የኳስ ቁጥጥር ብልጫ ላይ መሰረት ያደረገ አጨዋወት የሚከተሉት ሲዳማ ቡናዎች በነገው ጨዋታም ከዳዊት ተፈራ በቀጥታ ወደ ሀብታሙ ገዛሀኝ እና አዲስ ግደይ በሚላኩ ኳሶች እድሎችን ለመፍጠር ሊሞክሩ እንደሚችሉ ይገመታል።ሁለት ተከታታይ ጨዋታዎችን ማሸነፍ ያልቻሉት መቐለ 70 እንደርታዎች ከጨዋታው ነጥብ ይዘው የመውጣት ግዴታ ውስጥ ሆነው ጨዋታውን ያደርጋሉ። ባለፋት ጨዋታዎች ላይ በጉዳት ያልተሰለፈው ዮናስ ገረመው ወደ ሜዳ ሲመለስ አንጋፋው ተጨዋች ሚኪኤለ ደስታ አሁንም በጉዳት ምክንያት ከጨዋታው ውጪ ነው።
ወልዋሎ ከ ጅማ አባጅፋር
ዋና ዳኛ ፡ ኢንተ አርቢ በአምላክ ተሰማ
ሶስት ተከታታይ ጨዋታዎችን በማሸነፍ የሊጉ አናት ላይ የሚገኙት ወልዋሎ ና ገና በመሰራት ላይ ያሉት ጅማ አባጅፋሮችን የሚያገናኘው ይህ ጨዋታ ጥሩ ፋክክር ሊታይበት እንደሚችል ይገመታል።
የዮሐንስ ሳህሌ ቡድን ወልዋሎ አቼምፖንግ አሞስን በጉዳት ለነገው ጨዋታ ማይደርስ ሲሆን የፍቃዱ ደነቀ ና ካርሎስ ዳምጠው መድረስም አጠራጣሪ ሆኗል። ጅማ አባጅፋሮች በበኩላቸው ባለፋት ጨዋታዎች በስራ ፍቃድ ምክንያት ያልተጠቀሙባቸውን 3 ተጨዋቾች ለነገው ጨዋታ እንደሚደርሱላቸው ለማወቅ ተችሏል።