በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 7ጨዋታዎች የተደረጉ ሲሆን 6ቱ በክልል አንዱ ደግሞ አዲስ አበባ ላይ ተደርገዋል። ከነዚህ ጨዋታዎች መካከል ሁለቱን በዚህ ሪፖርት ለእናንተ እንዲስማማ አድርገን አቅርበንላችኋል።
ጨዋታ 1 ወልቂጤ ከተማ ከ ሰበታ ከተማ
9:00 ሲል የጀመረው እና በኢንተርናሽናል አርቢትር ብሩክ የማነብርሃን የተመራው የወልቂጤ ከተማና ሰበታ ከተማ ጨዋታ በእንግዳዎቹ ሰበታ ከተማዎች 1-0 አሸናፊነት ተጠናቋል። ሰበታ ከተማ በሊጉ የመጀመሪያውን ድል ለማስመዝገብ እንዲሁም ወልቂጤ ከተማ በሶስተኛው ሳምንት ያስመዘገበውን ድል ለመድገም የሚያደርጉት ጨዋታ በመሆኑ ከጨዋታው ቀድሞ በጉጉት እንዲጠበቅ አድርጎት ነበር። በመሆኑም ሰበታ ከተማ ወደ ወልቂጤ በመጓዝ 1-0 በሆነ ውጤት በማሸነፍ መመለስ ችሏል። አስቻለው ግርማ 8ኛው ደቂቃ ላይ ያስቆጠራት ግብ ለሰበታ በአመቱ የመጀመሪያ ድሉን እንዲያስመዘግብ አስችሎታል።
ውጤቱንም ተከትሎ ሰበታ ከተማ በ4 ነጥቦች 11ኛ ደረጃ ላይ ሲገኝ ወልቂጤ ከተማ በበኩሉ በእኩል 4ነጥቦች በ1 ግብ ክፍያ በልጦ 10ኛ ደረጃ ላይ መቀመጥ ችሏል።
ጨዋታ 2 ባህርዳር ከተማ ከ ድሬዳዋ ከተማ
በሌላ የክልል ላይ ጨዋታ ባህርዳር ላይ የተካሄደውና ባህርዳር ከተማን ከ ድሬዳዋ ከተማ ያገናኘው ጨዋታ በባህርዳር 4-1 አሸናፊነት ተጠናቋል። ባህርዳር ከተማ በጨዋታው የመጀመሪያውን ግብ ለማስቆጠር የፈጀበት 4ደቂቃዎች ብቻ ነበር። 4ኛው ደቂቃ ላይ ፍፁም ዓለሙ ግብ አስቆጥሮ ባህርዳር ከተማን ቀዳሚ ማድረግ ችሎ ነበር። ከግቡ መቆጠር 18 ደቂቃዎች በኋላ 22ኛው ደቂቃ ላይ ሪችሞንድ አዶንጎ ግብ አስቆጥሮ ድሬዳዋ ከተማን አቻ ማድረግ ችሎ ነበር። ሆኖም ግን አቻ ውጤቱ የቀጠለው ለ1ደቂቃ ብቻ ነበር 23ኛው ደቂቃ ላይ ማማዱ ሲዴቤ ሌላ ግብ አስቆጥሮ ባህርዳር ከተማን ወደ ቀድሞ መሪነቱ መመለስ ችሏል። በዚህም የመጀመሪያው አጋማሽ ተጨማሪ ግብ ሳይስተናገድበት ተጠናቋል። በሁለተኛው አጋማሽ ባህርዳር ከተማ 2ግቦችን ማስቆጠር ሲችል 73ኛው ደቂቃ ማማዱ ሲዴቤ ለራሱ ሁለተኛ ለቡድኑ 3ኛ ግብ ማስቆጠር ሲችል ከ2ደቂቃዎች በኋላ 75ኛው ደቂቃ ላይ ፍፁም ዓለሙ በተመሳሳይ ለራሱ ሁለተኛ ለቡድኑ 4ኛ ግብ አስቆጥሮ ጨዋታው በባህርዳር 4-1 አሸናፊነት ተጠናቋል።
ውጤቱንም ተከትሎ ባህርዳር ከተማ ከመሪው ወልዋሎ አ.ዩ. በ3 ነጥቦች ብቻ ዝቅ ብሎ በ7ነጥቦች 3ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ድሬዳዋ ከተማ በ3 ነጥቦች ወደ ወራጅ ቀጠና የገባ ሲሆን 14ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል።
ሊጉን ወልዋሎ አ.ዩ. በ10 ነጥቦች ሲመራ ፋሲል ከተማ፣ ባህርዳር ከተማ፣ ሀዋሳ ከተማ እና መቐለ 70 እንደርታ በእኩል 7ነጥቦች በግብ ክፍያ ተበላልጠው ከ2ኛ እስከ 5ኛ ያለውን ደረጃ ይዘዋል። የኮከብ ጎል አግቢነቱን ደግሞ የፋሲል ከተማው ሙጂብ ቃሲም በ4 ግቦች ሲመራ አዲስ ግደይ፣ ዳዋ ሁቴሳ እና ሰመረ ሀፍተይ በእኩል 3ግቦች ተከታዩን ደረጃ ይዘዋል።
አስተያየት ይስጡ