የደርቢነት ድባብ ተላብሶ በግዙፋ ትግራይ ስታድየም የተካሄደው የመቐለ 70 እንደርታና የወልዋሎ ዓድግራት ዩኒቨርሲቲ ጨዋታ በሚኪኤለ ደስታና ሳሙኤል ሳሊሶ ሁለት ግቦች በምዓም እምበሳዎቹ እሸናፊነት ተጠናቋል።

የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ፕሬዝዳንት ኢሳያስ ጅራ እና ምክትል ፕሬዝዳንት ኮሎኔል አወል አብዱራሂም በእንግድነት በተገኙበት በዛሬው ጨዋታ በጸጋይ ኪዳነ ማርያም ሚመሩት ወልዋሎዎች ባለፈው ሳምንት በሃዋሳ ከተሸነፈው ቡድናቸው ዳንኤል አድሃኖምን በእንየው ካሳሁን፣ዮውሃንስ ሽኩሩን በበረከት አማረ፣ዋለልኝ ገብሬን በፕሪንስ ሰርቪንሆ፣ዳዊት ፍቃዱን በኤፍሬም አሻሞ ባጠቃላይ አራት ተጨዋቾችን ሲቀይሩ መቐለዎችም ቢያድግልኝ ኤልያስ በስዩም ተስፋዬ፣አንተነህ ገ/ክርስቶስ በያሬድ ሃሰን፣ዮናስ ገረመውን በያሬድ ከበደ ቀይረው ወደ ሜዳ ገብተዋል ።

ተቀያያሪ የኳስ ብልጫ የታየበት የመጀመርያው 45 በሁለቱም በኩል ለግብነት የቀረቡ እድሎችን መፍጠር የቻሉበት ነበር፤ወደ ቀኝ መስመር እድልተው ሲያጠቁ የነበሩት ቢጫ ለባሾቹ ወልዋሎዎች በእንየው ካሳሁንና፣አፈወርቅ ሃይሉ እማካኝነት ለግብ የቀረቡ ሙከራዎችን ቢያደርጉም ኢላማቸውን የጠበቁ ኣልነበሩም።በገ/መድህን ሃይለ ሚመሩት መቐለ 70 እንደርታ በያሬድ ከበደና አማኑኤል ገ/ሚካኤል መካከል በተፈጠረው የቆየ ጥምረት በመጠቀም ፈጣን ጥቃቶችን በወልዋሎ ዓድግራት ዩኒቨርሲቲ ተከላካዮች ላይ ሲፈጽሙ ታይቷል፤የዚህ የተጠና ማጥቃት ውጤትም ጨዋታው በተጀመረ በ30ኛው ደቂቃ ከያሬድ ከበደ የተላከለትን ኳስ ቀኝ መስመር ላይ የተሰለፈው እማኑኤል ገ/ሚካኤል ሞክሮት በረከት አማረ ወደ ውጭ ሊወጣ ከቻለው ኳስ የተገኘውን የማእዘን ምት ሚካኤል ደስታ(ጣልያኑ) በቀጥታ በመምታት መቐለን መሪ በማድረግ የመጀመርያ 45 እንዲጠናቀቅ አድርጓል።
ሁለተኛው 45 ወልዋሎዎች ኣቻ ሚያደርጋቸውን ግብ ለማስቆጠር መቐለዎችም መሪነታቸውን ለማስቀጠል ሃይል የተቀላቀለበት እና እግር ኳሳዊ የሆነ ውጥረት የታየበት ጨዋታ እሳይተዋል። በ4-3-3 አሰላለፍ(ኳስ ሲነጠቁ ወደ 4-5-1 በሚቀየር) አሰላለፍ የተጠቀሙት ወልዋሎዎች 50ኛው ደቂቃ ላይ በመቐለ 70 እንደርታ ተከላካይ ክፍል ስህተት የተገኛውን ግልጽ የግብ አጋጣሚ ሪችሞንድ ኦዶንግ ከፊሊፕ ኦቮኖ ጋር ፊትለፊት ቢገናኝም ኢኳቶሪያል ጊናዊው ግብ ጠባቂ ኣድኖበታል።

4-2-3-1 አሰላለፍን ከመጀመርያው 45 በተለየ መልኩ ሚኬኤል ደስታና ሻይቡ ጅብሪልን ወደ ራሳቸውን ወደ ፊት የሜዳ በመመለስ ፊት ላይ በተሰለፋት(እማኑኤል ገ/ሚካኤል፣ያሬድ ከበደ እና ሳሙኤል ሳሊሶ) ኣማካኝነት ጥቃት ለመሰንዘር ሲሞክሩ ተስተውሏል ።ለመቐለ 70 እንደርታ ሁለተኛ የኢትዮጵያ ፕሪሜየር ሊግ ጨዋታውን ያደረገው ሳሙኤል ሳሊሶ በ65ኛው ደቂቃ ላይ ፍጹም ቅጣት ሳጥን ውስጥ በግራ መስመር በኩል ያገኘውን ኳስ በጥሩ ኣጨራረስ በማስቆጠር የመቐለ ግብን ወደ ሁለት ከፍ ማድረግ ችሏል።ሁለተኛው ግብ ከተቆጠረ በኃላ ወልዋሎዎች የተጨዋቾችን ቅያሪ በማድረግ ወደ ጨዋታው ለመመለስ ቢሞክሩም ጣጣቸውን የጨረሱ የግብ እድሎችን መፍጠር ሳይችሉ ጨዋታው በመቐለ 70 እንደርታ አሸናፊነት ተጠናቋል።

በዚህም ውጤት መሰረት መቐለ 70 እንደርታ ተከታታይ ሁለት ጨዋታዎች ሙሉ ስድስት ነጥብ ማሳካት ችለዋል።
አስተያየት ይስጡ