ቅዱስ ጊዮርጊስ ሽረ ላይ ነጥብ ተጋርቶ ከተመለሰበት ጨዋታ ቅጣት ላይ በሚገኘው ሳላዲን በርጌቾ እና አሜ መሀመድ ምትክ ኢሱፍ ቡርሀና እና ሀምፍሬይ ሚዬኖን የተጠቀመ ሲሆን በተመሳሳይ ሁለት ለውጦች ያደረጉት ሲዳማዎችም አዳማን ከረቱበት ጨዋታ በአምስተኛ ቢጫ ካርድ ባልተሰለፈው ግርማ በቀለ እና ዳዊት ተፈራ ቦታ ተስፉ ኤልያስ እና ትርታዬ ደመቀን ተጠቅመዋል።
የመጀመሪያው አጋማሽ በአብዛኛው የባለሜዳዎቹ የበላይነት የታየበት ነበር። ሁለቱም ተጋጣሚዎች መሀል ሜዳ ላይ የተረጋጉ ቅብብሎችን በብዛት መከወን ባልቻሉበት በዚህ አጋማሽ የሜዳ ላይ ግጭቶችም ተበራክተው ታይተዋል። በቶሎ ኳሶችን ወደ መስመር በማሳለፍ ወደ ቀኝ አድልተው ጫና ፈጥረው የነበሩት ሲዳማዎች 7ኛው ደቂቃ ላይ ከግሩም አሰፋ በተነሳ ረጅም ኳስ ሀብታሙ ገዛኸኝ ከሳጥን ውስጥ ካደረገው ኢላማውን ያልጠበቀ ሙከራ በኋላ በማጥቃቱ ተቀዛቅዘው ታይተዋል።

ወደ ፊት የሚላኩ ኳሶች ያልተመጠኑ መሆን እና የቡድኑ የአማካይ ክፍል በሽግግሮች ወቅት ይታይበት የነበረው መበታተን ደግሞ ለተወሰደባቸው ብልጫ ምክንያቶች ተደርገው የሚወሰዱ ናቸው።
ቅዱስ ጊዮርጊሶች እንደተጋጣሚያቸው ሁሉ ኳስ ይዘው ባይጫወቱም ከኋላ ከሚነሱ ረጃጅም ኳሶቻቸው በተጨማሪ ከአማካዮቹ በቂ ሽፋን ሳያገኝ በቀረው የሲዳማ የተከላካይ መስመር መሀል በሚፈጠሩ ክፍተቶች ደጋግመው በሳጥን ውስጥ መገኘት ችለው ነበር። በተለይም አቤል ያለው 20ኛው ደቂቃ ላይ በቀኝ በኩል ሰብሮ ገብቶ ያመከነው እና 32ኛው ላይ ሚዮኔ ከሰነጠቀለት ኳስ ከግብ ጠባቂ ጋር ተገናኝቶ የሳተው በዚህ ረገድ ተጠቃሽ ነበሩ። አቤል 21ኛው ደቂቃ ላይም ኢሱፍ ብርሀና በግራ በኩል ካደረሰው ኳስ ከቅርብ ርቀት ሞክሮ ተከላካዮች ተደርበው ከውጥቶታል።

ሁለተኛው አጋማሽ ሲጀምር ሰንደይ ሙቱኩ እና ዳዊት ተፈራን ቀይረው በማስገባት የኋላ እና የመሀል ክፍላቸውን ለማስተካከል ጥረት ያደረጉት ሲዳማዎች መጠነኛ ለውጥ ቢታይባቸውም አሁንም የመጨረሻ የግብ ዕድሎችን መፍጠር አልሆነላቸውም። ከኋላ በሚጣሉ ኳሶች ላይ ተመስርተው በግል ጥረታቸው አጋጣሚዎችን ለመፍጠር ሲሞክሩ የነበሩት አዲስ ግደይ እና ሀብታሙ ገዛኸኝ እንቅስቃሴዎችም ፍሪያማ ካለመሆናቸው ባለፈ የመሀል አጥቂው መሀመድ ናስርም ተቀይሮ እስከወጣበት ጊዜ ድረስ ተነጥሎ ቆይቷል። በተደጋጋሚ በተጋጣሚያቸው ሳጥን ውስጥ እየተገኙ ሙከራዎችን ለማድረግ ከጫፍ ሲደርሱ ይታዩ የነበሩት ጊዮርጊሶችም የፈፅሟቸው በነበሩ ይቅብብል እና የሙከራ ውሳኔ ስህተቶች ምክንያት ጥረቶቻቸው የማዕዘን ምቶችን ከማስገኘት ባለፈ ፍቅሩ ወዴሳን የሚፈትኑ አልነበሩም።
በ80ኛው ደቂቃ ላይ አሜ መሀመድ በተከታታይ ሁለት ኳሶችን ከሳጥን ውጪ ሲሞክር አንዱ በግቡ አግዳሚ ሌላኛው ደግሞ በፍቅሩ ጥረት ድነዋል። ሆኖም ከሦስት ደቂቃዎች በኋላ ሜንሱ ከግራ መስመር ያሻማውን ኳስ ሰንደይ ሙቱኩ ፍቅሩ ይደርስበታል በሚል በተዘናጋበት ቅፅበት አቡበከር ሳኒ ከኋላ በመግባት በግንባሩ አስቆጥሮ ጨዋታው በቅዱስ ጊዮርጊስ 2-0 አሸናፊነት ተጠናቋል።

አስተያየት ይስጡ