በ33ኛዉ የካሜሩን የአፍሪካ ዋንጫ ከዘጠኝ አመታት በኋላ በመድረኩ ላይ እየተሳተፉ የሚገኙት የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን (ዋልያዎቹ) የምድብ የመጀመሪያ ጨዋታቸዉን በኬፕ ቨርዲ አቻቸዉ አንድ ለዜሮ በሆነ ዉጤት መሸነፋቸው ይታወሳል።
በምድቡ ሁለተኛ ጨዋታ ዛሬ ምሽት አዘጋጇን ሀገር ካሜሩንን ከሚገጥመዉ የዋልያዎቹ ስብስብ ዉስጥ በመጀመሪያው ጨዋታ ላይ በጉዳት ምክንያት ያልተሰለፈዉ አማካዩ ሽመልስ በቀለ ከጉዳቱ ማገገም ባለመቻሉ ምክንያት እንዲሁም ግብ ጠባቂዉ ፋሲል ገ/ሚካኤል በትከሻ ህመም ምክንያት ለምሽቱ ጨዋታ ዝግጁ ሳይሆኑ ቀርተዋል። በአንፃሩ በመጀመሪያው ጨዋታ ላይ መጠነኛ ጉዳት አስተናግዶ የነበረዉ ዳዋ ሁቴሳ ለጨዋታው ሙሉ በሙሉ ዝግጁ መሆኑ ተረጋግጧል።
ከምሽቱ ተጠባቂ ጨዋታ አስቀድሞ ቁጥሮች ስለሁለቱ ሀገራት ምን ይላሉ :-
ካሜሩን እና ኢትዮጵያ ከዚህ ቀደም አንድ ጊዜ ብቻ የተገናኙ ሲሆን ይኸዉም በ1970 የውድድር አመት በምድብ ጨዋታ ነበር ጨዋታዉንም ካሜሮን 3-2 በሆነ ዉጤት አሸንፋለች።
- ማሰታውቂያ -
ካሜሩን የመጀመሪያ ጨዋታዋን ቡርኪናፋሶን 2ለ1 ማሸነፏ ይታወሳል። ከዚህ ቀደም በ2006 ሁለቱን መክፈቻ ጨዋታቸዉን ማሸነፍ ችለዉ ነበር አንጎላን 3ለ1 እንዲሁም ቶጎን 2ለ0 በሆነ ዉጤት።
ካሜሩን በወርሀ ጥር 2015 በኮትዲቫር ከደረሰባት የመጨረሻ ሽንፈት በኋላ በአፍሪካ ዋንጫዉ ያደረገቻቸውን ያለፉት ሰባት የምድብ ጨዋታዎች አልተሸነፈችም 3 አሸንፋ 4 ደግሞ በአቻ ዉጤት አጠናቃለች።
ዋልያዎቹ በአፍሪካ ዋንጫዉ የመጀመሪያ ጨዋታ በኬፕ ቨርዴ 1ለ0 በሆነ ዉጤት ከተሸነፉ በኋላ ባለፉት 9 የአፍሪካ ዋንጫ ጨዋታዎች አንዱንም ማሸነፍ አልቻሉም 3 አቻ 6 ተሸነፉ።