የቅዱስ ጊዮርጊስ ስፖርት ማህበርን የአስተዳደር፣የማርኬቲንግና ፕሮሞሽን ዘርፍን ለማዘመንና ለማሻሻል የሚስችል ጥናት ለማስራት በዛሬዉ ዕለት ስምምነት ተፈራረመ።
ስምምነቱን ዛሬ ከሰዓት የክለቡ ፕሬዝዳንት አቶ አብነት ገብረመስቀልና የድንቅ ኢትዮጵያ ብራንድ ኮንሰልታት ኩባንያ ስራ አስኪያጅ አቶ ኤርሚያስ አየለ በስፖርት ማህበሩ መዝናኛ ማእከል በመገኘት ተፈራርመዋል፡፡
ጥናቱ ከዚህ ቀደም የቅዱስ ጊዮርጊስ ይከተል የነበረውን የክለብ የሰው ሃይል አስተዳደርና መዋቅር ፣እንዲሁም በገበያና ፕሮሞሽን ረገድ የአሰራር ስርዓቱን በመቀየር ክለቡን ለማዘመን ከፍ ያለ ጠቀሜታ እንደሚኖረው የክለቡ ፕሬዚዳንት አቶ አብነት ገብረመስቀል በስነ ስርዓቱ ላይ ገልፀዋል።
“ይህ ጥናት መደርደሪያ ላይ የሚቀመጥ ሳይሆን ወደ ተግባር የሚቀየር ነው” ያሉት ፕሬዝዳንቱ “በጥናቱ በሚቀርበው ምክር ሃሳብ መሰረት በጊዮርጊስ ውስጥ መለወጥ ያለባቸው የአሰራር ስርዓቶች በሙሉ ይቀየራሉ ” ሲሉም ገልጸዋል፡፡
የድንቅ ኢትዮጵያ ብራንድ ኮንሰልታት ኩባንያ ስራ አስኪያጅ አቶ ኤርሚያስ አየለ ድርጅታቸው አጠቃላይ ጥናቱን በ9 ወራት ጊዜ ውስጥ አጠናቆ ለክለቡ እንደሚያስረክብም ገልጸዋል። በተጨማሪም ላለፉት ወራትም ስለክለቡ አስፈላጊ የሚባሉ መረጃዎችን ለማሰባሰብ ከቦርዱና ከጽህፈት ቤቱ ሰራተኞች ጋር ውይይት መደረጉን ጠቅሰዋል፡፡

“ቅዱስ ጊዮርጊስ ከራሱ የሚተርፍ የስፖርት መሰረተ ልማት ባለቤት ነው” ያሉት አቶ ኤርሚያስ “ጥናቱ ክለቡ ያለውን አቅም በመጠቀም ወደ ተሻለ ደረጃ ለማሳደግ እንደሚረዳም” ገልጸዋል፡፡
በዚህ ጥናት ውስጥም ቅዱስ ጊዮርጊስ ካሉት ደጋፊዎች ባሻገር አዳዲስ ደጋፊዎችን ወደ ክለቡ ለመሳብና ደጋፊዎች ከክባቸው ጋር ያላቸውን ግንኙነት ለማጠናከርም የሚጠቅም እንደሆነ ተገልጿል።
© saint George S.A
አስተያየት ይስጡ