👉የክለቡ አመራሮች ውሳኔያቸውን ግልጽ አላደረጉም
ሰበታ ከተማ አሰልጣኙ ዘላለም ሽፈራውን ቡድኑ ካለበት ድሬዳዋ ከተማ ቢመልሰውም ውሳኔውን ማሳወቅ አልቻለም።
ሰበታ ከተማ በአዲስ አበባ ከተማ የደረሰበትን የ5ለ1 ሽንፈት ተከትሎ አሰልጣኙ ዘላለም ሽፈራውን ወደ ሰበታ እንዲመለስ በማድረግ ለዛሬ ጠዋት 4 ሰአት ቀጠሮ ይዘው የተነጋገሩ ቢሆንም ከቀጠሮው አንድ ሰዓት ዘግይተው የመጡት የክለቡ ፕሬዝዳንት አቶ ቶሎሳ የክለቡን ቦርድ ውሳኔን በግልጽ ሳይገልጹለት መለያየታቸውን ከታማኝ ምንጭ የተገኘው መረጃ ያስረዳል።
አሰልጣኝ ዘላለም ሽፈራው ቀሪ የሁለት አመት ተኩል ኮንትራት ያለው ሲሆን ከአሰልጣኙ የሚቀርብላቸውን የካሳ ክፍያ የሰጉ የሚመስሉት አመራሮቹ እንደገና ተነጋግረው ውሳኔያቸውን ለማሳወቅ የመረጡ ይመስላል። በጉዳዩ ዙርያ ጥያቄ የቀረበለት አሰልጣኝ ዘላለም ሽፈራው ከፕሬዝዳንቱ ጋር መገናኘቱን አምኖ ቁርጥ ያለ ውሳኔ አለማግኘቱንና ውሳኔያተውን እንዲያሳውቁት እየጠበቀ መሆኑ ተናግሯል። ከአሰልጣኙ ጋር አዲሱ የክለቡ የቴክኒክ ዳይሬክተር ፍቅሩ ተፈራም ወደ ሰበታ መጠራቱ ታውቋል።በጉዳዩ ዙሪያ የክለቡን ምላሽ ለማወቅ ወደ ፕሬዝዳንቱ አቶ ቶሎሳ የግል ስልክ ብንደውልም ስልኩ ባለመነሳቱ ምላሹን ማወቅ አልቻለንም።
ይህ በእንዲህ እንዳለ ሰበታ ከተማ የሚያደርጋቸውን ጨዋታዎችን እንዲመሩ ታግደው የነበሩት ምክትል አሰልጣኞች ብርሃኑ ደበሌና ዳንኤል ገብረማሪያም ድሬዳዋ የደረሱ ሲሆን የዋና አሰልጣኙ ዘላለም ሽፈራውን ወደ ሰበታ መጠራት የሰሙት ድሬዳዋ ከደረሱ በኋላ መሆኑ ታውቋል። “ወደ ሰበታ ያመጣኝ አሰልጣኝ ዘላለም በሌለበት አልሰራም ደስተኛም አይደለሁም”
በማለት አሰልጣኝ ዳንኤል ገ/ማሪያም ወደ አዲስአበባ እየተመለሰ መሆኑ ታውቋል።ሰበታ ከተማ በ14ኛ ሳምንት መርሃግብር በቀድሞ አሰልጣኙ አብርሃም መብራቱ የሚሰለጥነውን ባህርዳር ከተማን ይገጥማል።
አስተያየት ይስጡ