በቤትኪንግ ኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ23ተኛ ሳምንት መርሐግብር የመጨረሻ ዕለት ጨዋታ መቻል የሊጉን መሪ ቅዱስ ጊዮርጊስ 1ለ0 በሆነ ዉጤት ማሸነፍ ችሏል።
ተከታዩ ባህርዳር ከተማ በሳምንቱ መርሐግብር ጨዋታውን ማሸነፉን ተከትሎ ቅዱስ ጊዮርጊስ የነጥብ ልዩነቱን ዳግም ወደ ሰባት ከፍ ለማድረግ እና በተቃራኒው በደረጃ ሰንጠረዡ ከወገብ በታች ይገኝ የነበረዉ መቻል ደግሞ ነጥቡን ወደ ሰላሳ ሁለት ከፍ በማድረግ ወደ ወደ ሰንጠረዡ አናት ከሚገኙት ክለቦች ተርታ ለመመደብ ባደረጉት ጨዋታ ሁለቱም ክለቦች ጥሩ የሚባል ለዕይታ ማራኪ የሆነ የጨዋታ እንቅስቃሴን ሲያስመለክቱ ተስተውሏል።
በዚህ ሂደት በጀመረዉ የዕለቱ መርሐግብርም በ14ኛዉ ደቂቃ ላይ መቻሎች ሙከራ ማድረግ ችለዋል። በዚህም ሄኖክ አዱኛ ከቀኝ መስመር በኩል ወደ ሳጥኑ ያሻማዉን ኳስ አህመድ ረሽድ ሲመልሰዉ በመልሶ ሚጥቃት በቶሎ የፈረሰኞቹ ሳጥን ውስጥ መድረስ የቻሉት መቻሎች በእስራኤል እሸቱ አማካኝነት ድንቅ ሙከራ ማድረግ ቢችሉም ኳሷ ለጥቂት ወደ ዉጭ ወጥታለች።
በጨዋታዉ የመሐል ክፍሉን በመቆጣጠር አደጋ ለመፍጠር ሲጥሩ የነበሩት ፈረሰኞቹ በሙከራ ረገድ ተቸግረዉ የነበረ ሲሆን ኢላማዉን የጠበቀ ሙከራ ለማድረግም 40 ያህል ደቂቃዎችን መጠበቅ ግድ ብሏቸዋል። በዚህም አማካዩ ዳዊት ተፈራ ከቀኝ በኩል የተሰጠዉን ቅጣት ምት በቀጥታ ወደ ግብ ሞክሮ የነበረ ቢሆንም ኳሷ እንደምንም በግቡ አናት ወጥታለች። የመጀመሪያዉ አጋማሽ ሊገባደድ ጥቂት ደቂቃዎች በቀሩት ወቅትም መቻሎች በሳሙኤል አስፈሪ አማካኝነት ከቅጣት ምት ጥሩ ሙከራ አድርገዉ የነበረ ቢሆንም ግብ ጠባቂዉ ባህሩ ነጋሽ ኳሷን ወደ ዉጭ አውጥቷታል።
- ማሰታውቂያ -
ከዕረፍት መልስ በንፅፅር በጥሩ የማጥቃት እንቅስቃሴ ወደ ሜዳ የተመለሱት ፈረሰኞቹ አጋማሹ እንደተጀመረ ወዲያዉኑ ጥሩ ዕድል መፍጠር ችለዉ ነበር ፤ በዚህም ሄኖክ አዱኛ ወደ ሳጥን ያሻማዉን ኳስ ረመዳን የሱፍ በቀጥታ ወደ ግብ ሞክሮ የነበረ ቢሆንም ተከላካዩ አህመድ ረሽድ ኳሷን ተደርቦ አውጥቷታል።
በሁለተኛዉ አጋማሽም ወደ መከላከሉ አድልተዉ የተመለሱት መቻሎች በ62ኛዉ ደቂቃ ላይ ግብ ማስቆጠር ችለዋል። በዚህም ተከላካዩ ሄኖክ አዱኛ ላይ ጥፋት መስራቱን ተከትሎ የተሰጠዉን ፍፁም ቅጣት ምት የግራ መስመር አጥቂው ከንዓን ማርክነህ ወደ ግብነት በመቀየር ክለቡን መሪ ማድረግ ችሏል።
ግብ ከተቆጠረባቸዉ በኋላ ወደ ጨዋታዉ ለመመለስ እና በቶሎ የአቻነት ግብ ለማስቆጠር ሲጥሩ የነበሩት ፈረሸኞቹ በ64ተኛዉ ደቂቃ ላይ ጥሩ የሚባል ለግብ የቀረበ ሙከራን ማድረግ ችለዋል። በዚህም አጥቂዉ እስማኤል ኦሮ አጎሮ ላይ የተሰራውን ጥፋት ተከትሎ የተገኘዉን ቅጣት ምት ሄኖክ አዱኛ በቀጥታ ወደ ግብ ሞክሮ የነበረ ቢሆንም ግብ ጠባቂዉ ዉብሸት ጭላሎ እንደምንም ተቆጣጥሯታል።
የጨዋታዉ ሰዓት እየገፋ በመጣ ቁጥር የማጥቃት ጫናቸዉን አበርትተዉ የቀጠሉት ጊዮርጊሶች በጨዋታዉ መገባደጃ ሰዓት ላይ ተቀይሮ በገባዉ አዲስ ግደይ አማካኝነት ጥሩ ሙከራ ማድረግ ቢችሉም ግብ ማስቆጠር ሳይችሉ ቀርተዉ በመቻል 1ለ0 በሆነ ዉጤት ተሸንፈዋል። ዉጤቱን ተከትሎ መቻል በ32 ነጥብ ሰባተኛ ደረጃ ላይ ሲቀመጥ ፤ በተቃራኒው ሽንፈት የገጠመዉ ቅዱስ ጊዮርጊስ ደግሞ በ51 ነጥቦች በመሪነት ስፍራ ላይ ተቀምጧል።