በ16ኛው ሳምንት የመጨረሻ ቀን ውሎ በቀዳሚነት የተደረገው የወላይታ ድቻ እና የድሬዳዋ ከተማ ጨዋታ ቃልኪዳን ዘላለም ባስቆጠረው ብቸኛ ግብ ወላይታ ድቻዎች ማሸነፍ ችለዋል ።
ወላይታ ድቻዎች በ15ኛው ሳምንት ወልቂጤ ከተማን በረቱበት ጨዋታ ላይ ከተጠቀሙት ምርጥ 11 አንድ ለውጥ ብቻ በማድረግ በረከት ወልደዮሐንስ ደጉ ደበበን ተክቶ እንዲገባ ያደረጉ ሲሆን በድሬዳዋ ከተማ በኩል ደግሞ በሳምንቱ በፋሲል ከተማ በሰፊ ውጤት በተሸነፉበት ጨዋታ ላይ በቋሚ አሰላለፍ ተካተው ከነበሩት ውሰጥ ስድስት ተጫዋቾችን በመቀየር ፍሬው ጌታሁን ፣ አማረ በቀለ ፣ ብሩክ ቃልቦሬ ፣ ጋዲሳ መብራቴ ፣ ሙኽዲን ሙሳ እና ማማዱ ሲዲቤ ጨዋታውን እንዲጀምሩ አድርገዋል ።
በተመሳሳይ የ4-3-3 አሰላለፍ ጨዋታቸውን የጀመሩት ሁለቱ ክለቦች በመሀል ላይ ብልጫ በመውሰድ ለመጫወት ፍላጎት የነበራቸው ሲሆን በአንፃራዊነት ድሬዳዋ ከተማዎች በተሻለ የኳስ ቁጥጥር የበላይነት እና ወደ ተጋጣሚ የግብ ክልል በመድረስ ከወላይታ ድቻ ተሽለው ታይተዋል ።
ድሬዳዋ ከተማዎች በተለይም ከመስመር በሚሻገሩ ኳሶች ወደ ወላይታ ድቻ ሳጥን ለመግባት እና የግብ ዕድሎችንም ለመፍጠር በተደጋጋሚ ሲሞክሩ ነበር ። በአንፃሩ ከመሪው ቅዱስ ጊዮርጊስ ላለመራቅ ጨዋታውን ማሸነፍ የግድ የሚላቸው የጦና ንቦቹ በአጋማሹ ወደ ድሬዳዋ የግብ ክልል ለመድረር በአጅጉ ተቸግረው የነበረ ሲሆን ለፊት አጥቂው ስንታየሁ መንግስቱ የሚላኩ ኳሶችም ጥሩ የሚባሉ አልነበሩም ።
በ36ኛው ደቂቃ ላይ ጋዲሳ መብራቴ ከቀኝ መስመር በመነሳት ወደ ግብ አክርሮ የመታው ኳስ የግቡን አግዳሚ ለትሞ ወደ ውጪ ሲወጣ በ42ኛው ደቂቃ ደግሞ አማረ በቀለ ከግራ መስመር ወደ ሳጥኑ ያሻገረውን ኳስ አጥቂው ማማዱ ሲዲቤ ጀርባውን ለግብ ሰጥቶ አግኝቶት የነበረ ሲሆን ዞሮ ወደ ግብ ሞክሮት በግብ ጠባቂው ፅዮን መርዕድ ተመልሷል ።
አጋማሹ መጠናቀቂያ ደቂቃዎች ላይ በወላይታ ድቻ በኩል ያሬድ ዳዊት ከረጅም ርቀት ላይ የተገኘውን የቅጣት ምት ወደ ግብ ሲያሻግረው ያገኘው አንተነህ ጉግሳ በግንባር ወደ ግብ ልኮት የድሬደዋ ከተማው የግብ ዘብ ፍሬው ጌታሁን ግብ ከመሆን አድኖታል ። የመጀመሪያው አጋማሽም ያለ ግብ አቻ ተጠናቀቀ ።
በሁለተኛው አጋማሽ መጀመሪያ ደቂቃዎች ላይ ድሬዳዋ ከተማዎች በመጀመሪያ አጋማሽ የነበራቸውን የኳስ ቁጥጥር የበላይነት በማስቀጠል ወደ ወላይታ ድቻ የግብ ክልል ቶሎ ቶሎ ለመድረስ የቻሉ ቢሆንም ፅዮን መርዕድን የፈተነ የግብ ሙከራ በማድረጉ ረገድ ግን ደካማ ነበሩ ።
በአንፃሩ ወደ ኋላ አፈግፍገው በመጫወት ላይ የነበሩት ወላይታ ድቻዎች አልፍ አልፎ በፈጣን መልሶ ማጥቃት ወደ ድሬዳዋ ከተማ የግብ ክልል ለመድረስ ጥረቶችን ያደረጉ ሲሆን በተጨማሪም ያሬድ ዳዊት ከቆሙ ኳሶች ወደ ግብ ክልል የሚያደርሳቸው ኳሶች ለጦና ንቦቹ ሌላ የግብ ዕድል መፍጠር የቻሉባቸው አጋጣሚዎች ነበሩ ።
በ54ኛው ደቂቃ ላይ የወላይታ ድቻው አምበል ያሬድ ዳዊት ከቀኝ መሰመር አቅጣጫ ወደ ግብ ክልል ያሻገረውን ኳስ ሀብታሙ ንጉሴ ነፃ ሆኖ አግኝቶት የነበረ ቢሆንም በግንባር የገጨው ኳስ ኢላማውን ሳይጠብቅ ቀርቷል ።
በ66ኛው ደቂቃ ላይ ወላይታ ድቻዎች መሪ መሆን የቻሉበትን ግብ አግኝተዋል ። በተደጋጋሚ ወደ ግብ ክልል በግሩም ሁኔታ የሚያደርሳቸው ኳሶች በቡድን አጋሮቹ ወደ ግብ ሊቀየሩለት ያልቻለው ያሬድ ታደሰ በተጠቀሰው ደቂቃ ላይ ከቅጣት ምት ወደ ግብ ያሻገረውን ኳስ የድሬዳዋ ከተማ ተጫዋቾች ወጥቷል ብለው በተዘናጉበት ወቅት አናጋው ባደግ ደርሶ ያቀበለውን ኳስ ነፃ ሆኖ በግቡ ትይዩ ቆሞ የነበረው ቃልኪዳን ዘላለም ማስቆጠር ችሏል ።
ከግቡ መቆጠር በኋላ ወላይታ ድቻዎች የኋላ መስመራቸውን በማጠናከር የድሬዳዋ ከተማን ኳሶች ማበላሸት የቻሉ ሲሆን የሚነጥቋቸውን ኳሶችም በረጅም ወደ ፊት መስመር በማድረስ ሌላ ግብ ለማግኘት ጥረቶችን ማድረግ ችለዋል ።
ድሬዳዋ ከተማዎች ምንም እንኳን ከመጀመሪያው ኳሱን ይዘው በመጫወት ወደ ሶሰትኛው የማጥቃት ዞን ለመድረስ ጥረቶችን ማድረጋቸውን ቢቀጥሉም ጋዲሳ መብራቴ በተጨማሪ ደቂቃዎች ላይ ካደረጋቸው ሁለት የግብ ሙከራዎች ውጪ ይህ ነው የሚባል የግቡ ሙከራ ማድረግ አልቻሉም ።
ተቀይሮ የገባው ምንይሉ ወንድሙ በመጨረሻ ሰከንዶች ላይ በመልሶ ማጥቃት ወደ ሳጥን ይዞ የገባውን ኳስ መጠቀም ሳይችል ከቀረ በኋላ የዓለምአቀፍ ዳኝ ሊድያ ታፈሰ የጨዋታ መጠናቀቂያ ፊሽካ ድምፅ ተሰምቷል ።
ውጤቱን ተከትሎ ወላይታ ድቻ ነጥቡን 31 በማድረስ ከመሪው ቅዱስ ጊዮርጊስ ጋር ያለውን የነጥብ ልዩነት ወደ 3 ማጥበብ የቻለ ሲሆን ተሸናፊው ድሬዳዋ ከተማ ደግሞ በነበረበት 13 ነጥብ እና 16ኛ ደረጃ ላይ ለመቆየት ተገዷል ።
በ17ኛ ሳምንት ጨዋታዎች ወላይታ ድቻ በመጪው አርብ ቀን 9 ሰዓት ላይ ሀዋሳ ከተማን ሲገጥም ድሬዳዋ ከተማ በበኩሉ አንድ ቀን ቀደም ብሎ ቀን በተመሳሳይ ሰዓት ሲዳማ ቡናን የሚገጥም ይሆናል ።
አስተያየት ይስጡ