በመጀመሪያዉ ሳምንት የቤትኪንግ ኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ መዝጊያ ጨዋታ መቻል እና ሀድያ ሆሳዕና ተገናኝተዉ መቻል 1ለ0 በሆነ ዉጤት በማሸነፍ የመጀመሪያ ጨዋታውን በድል ተወጥቷል።
በተመጣጣኝ ፋክክር በጀመረው የሁለቱ ክለቦች ጨዋታ ገና በመባቻዉ ለግብ የቀረበ ሙከራ ተመልክተንበታል። በዚህም በ2ኛዉ ደቂቃ ላይ ፍፁም አለሙ ከተሾመ በላቸዉ የተቀበለዉን ኳስ ወደ ግብ ሞክሮ የነበረ ቢሆንም ወጥታበታለች። በተደጋጋሚ በረጃጅም ከሚጣሉ ኳሶች አንዳች ነገር ለመፍጠር ሲጥሩ የነበሩት ሀድያዎች በ16ኛዉ ደቂቃ ላይ መሪ ሊሆኑ የሚችሉበት ዕድል ተፈጥሮ ነበር ፤ በዚህም ከግራ መስመር በኩል ሄኖክ አርፌጮ ያሻማዉን ኳስ ተከላካዩ ቶማስ ስምረቱ ለማዉጣት ሲሞክር ኳሷ ተጨርፋ ወደ ራሱ ግብ ልትቆጠር የነበረ ቢሆንም የግብ ዘቡ ተክለማርያም እንደምንም አዉጥቷታል።
- ማሰታውቂያ -
በሙከራ ረገድ ብዙም ሳቢ ባሌነበረዉ ጠዋታ መቻሎች የተሻለ የኳስ ቁጥጥር የነበራቸዉ ቢሆንም ነገር ግን ግብ ለማስቆጠርም ሆነ ለግብ የቀረበ ጠንካራ ሙከራ ለማድረግ ግን ሲተገሩ ተስተውሏል። በተቃራኒው በይበልጥ ወደ ራሳቸዉ የግብ ክልል አፈግፍገዉ በመጫወት የመቻሎችን የማጥቃት ሀይል ሲመክቱ የተስተዋሉት ሀድያዎች ምንም እንኳን በአጋማሹ ይህ ነዉ የሚባል ተጠቃሽ ሙከራ ማድረግ ባይችሉም ፤ ግባቸዉን ሳያስደፍሩ ወደ መልበሻ ክፍል አምርተዋል።
ከዕረፍት መልስ በጥቂቱም ቢሆን መሻሻል ይታይባቸዉ የነበሩት ሀድያዎች በተለይ በሜዳዉ የቀኝ ክፍል ላይ የጨዋታ ብልጫ መዉሰድ ቢችሉም ነገር በተመሳሳይ እንደ መጀመሪያዉ አጋማሽ ሁሉ ሙከራ ማድረግ ተስኗቸዉ ነበር ፤ በጥቂቱም ቢሆን የሁለተኛው አጋማሽ የመጀመሪያ ደቂቃዎች ላይ መቀዛቀዝ ተስተዉሎባቸዉ የነበሩት መቻሎች ግን በተለይ በጨዋታዉ በ59ኛዉ እና በ70ኛዉ ደቂቃ በምንይሉ ወንድሙ እና ከንዓን ማርክነህ ያደረጓቸዉ ሙከራዎች ድንቅ የነበሩ ቢሆንም ነገር ግን በሀድያዉ የግብ ዘብ ሲመክኑ ተስተውሏል።
በ80ኛዉ ደቂቃ ላይ ደግሞ የተገኘዉን ቅጣት ምት የሀድያው አጥቂ ባየ ገዛኸኝ ቀጥታ ወደ ግብ ሞክሮ የነበረ ቢሆንም በግብ ተባቂዉ ተክለማርያም ሻንቆ ድንቅ ብቃት ከሽፋለች። ከሁለት ደቂቃዎች በኋላ ግን የሀድያዉ ተመስገን ብርሐኑ ፍፁም አለሙ ላይ የሰራዉን ጥፋት ተከትሎ የተገኘዉን ፍፁም ቅጣት ምት አጥቂው ምንይሉ ወንድሙ ወደ ግብነት ቀይሮ መቻል የመጀመሪያውን ጨዋታ በድል እንዲወጣ ማድረግ አስችሏል።
በቀጣይ መቻል ከአዳማ ከተማ ጋር ሲገናኝ በተመሳሳይ ሀድያ ሆሳዕና ደግሞ ከሲዳማ ቡና ጋር የሚጫወቱ ይሆናል።