በሰባተኛ ሳምንት የመጨረሻ ጨዋታ ኢትዮጵያ ቡናን ከድሬዳዋ ከተማ አገናኝቶ በአቡበከር ናስር ሁለት ግቦች ቡናማዎቹ 2 ለ 0 በሆነ ውጤት አሸንፈዋል ።
ሁለቱም ክለቦች በስድስተኛው ሳምንት ጨዋታ ከተጠቀሙት ቋሚ አሰላለፍ በተመሳሳይ አንድ አንድ ቅያሪዎች ያደረጉ ሲሆን በድሬዳዋ ከተማ በኩል አቤል ከበደ እንዲሁም በኢትዮጵያ ቡና በኩል ግብ ጠባቂውን በረከት አማረን ቀይረው በማስገባት ጨዋታውን ጀምረዋል ።

በመጀመሪያው አጋማሽ ቡናማዎቹ በኳስ ቁጥጥሩ ብልጫ በመውሰድ የተጫወቱ ሲሆን በድሬዳዋ ከተማዎች በኩል በፈጣን በመልሶ ማጥቃት እና ረጃጅም ኳሶችን ለመጠቀም የግብ ዕድል ለመፍጠር ጥረት አድርገዋል ።
በጨዋታው 15ኛው ደቂቃ ላይ ሀይሌ ገብረትንሳይ ከቀኝ መስመር ያሻገረውን ኳስ የድሬደዋው ግብ ጠባቂ ፍሬው መቆጣጠር ሳይችል ቀርቶ አጠገቡ የነበረው አበበከር ናስር ኳሱን አግኝቶ ወደ ግብ ቢመታወም ተከላካዩ መሳይ ደርሶ የማዕዘን ምት አድርጎታል ።

በኳስ ቁጥጥሩ ብልጫ የነበራቸው ኢትዮጵያ ቡናዎች አቡበከር ናስርን ኢላማ ያደረጉ ኳሶችን ወደ ግብ ቢልኩም ጠንከር ያለ የግብ ሙከራ ማድረግ ተስኗቸው ነበር ። ድሬዳዋ ከተማዎች 40ኛ ደቂቃ ላይ ሙኸዲን ሙሳ ከመሀመድ የደረሰውን ኳስ ጠንከር አድርጎ ሳይመታው በመቅረቱ በረከት በቀላሉ ይዞታል ። የመጀመሪያው አጋማሽ ሊጠናቀቅ በተጨማሪ ደቂቃዎች ላይ ሳለ እንየው ካሳሁን በሳጥን ውስጥ ያገኘውን ኳስ በአግባቡ ሳይጠቀሙበት ቀርቷል ።
በሁለተኛው አጋማሽ በተመሳሳይ ልክ እንደመጀመሪያው አጋማሽ ሁሉ ቡናማዎቹ የበላይነት ያሳዩበት ነበር ። በዚህም 57ኛ ደቂቃ ላይ አቡበከር ናስር ከሳጥን ውጪ ወደ ግብ መቶ ያደረገው ጠንካራ ሙከራ በግብ ጠባቂው ፍሬው ተመልሶበታል ።

59ኛው ደቂቃ ላይ አቡበከር ናስር ከግራ መስመር ተነስቶ የድሬዳዋ ተጫዋቾችን በመሸወድ ወደ ግብ ልክ በገባበት ጊዜ በተሰራበት ጥፋት ቡናማዎቹ የፍፁም ቅጣት ምት አግኝተው የፍፁም ቅጣት ምቱን ራሱ አቡበከር ናስር 62ኛ አስቆጥሮ ኢትዮጵያ ቡናን መሪ ያደረገች ግብ አስቆጠረ ።


ግብ ያስተናገዱት ድሬዳዋ ከተማዎች የማጥቃት ሚና ያላቸው ተጫዋቾችን ቀይረው በማስገባት ጭምር ግብ ለማግኘት ያደረጓቸው ሙከራዎች ፍሬያማ ሳይሆኑ የቀሩ ነበሩ ። ጨዋታው ሊጠናቀቅ በተቃረበበት ጊዜ በሳጥን ውስጥ በአቡበከር ናስር ላይ በድጋሚ በተሰራ ጥፋት ቡናማዎቹ ሁለተኛ የፍፁም ቅጣት ምት አገኙ ። ልክ እንደመጀመሪያው ግብ ሁሉ አቡበከር ናስር ሁለተኛውን ግብ በማስቆጠር የቡናማዎቹ አሸናፊነት አስተማማኝ ማድረግ ቻለ ።

ይህም ሊጉ ከተጀመረ በኋላ በተከታታይ ጨዋታዎች ከግብ ርቆ የነበረው አቡበከር ናስር በሁለት ጨዋታዎች አራት ግቦችን በማስቆጠር ከከፍተኛ ግብ አስቆጣሪዎች ተርታ መመደብ ችሏል ።
ውጤቱን ተከትሎም ኢትዮጵያ ቡና ነጥቡን 11 በማድረስ ደረጃውን ወደ 6ኛ ያሳደረ ሲሆን ሽንፈት ያስተናገደው ድሬደዋ ከተማ በ8 ነጥብ ወደ 10ኛ ደረጃ ዝቅ ብሏል ።
አስተያየት ይስጡ