በሊጉ የሳምንቱ የሁለተኛ ቀን ጨዋታ ሲዳማ ቡና ፣ ኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ እና ፋሲል ከነማ ሲያሸንፍ የሀድያ ሆሳዕና እና ኢትዮጵያ ቡና ጨዋታ በበኩሉ በአቻ ውጤት ተፈፅሟል።

በአዲስ አበባው አበበ ቢቂላ ስታዲየም ቀን ሰባት ሰዓት ላይ ሲል አዳማ ከተማን ከኢትዮ ኤሌክትሪክ ባገናኘው ጨዋታ አዳማ ከተማዎች ከአሰልጣኝ ለውጡ በኋላ ሦስተኛ ተከታታይ ጨዋታቸውን ለመሸነፍ ተገደዋል። 42ኛው ደቂቃ ላይ ከቀኝ የሜዳው ክፍል ያሬድ የማነ ከቅጣት ምት በፍጥነት አስጀምሮ ከበዛብህ መለዮ ጋር ካደረገው ቅብብል በኋላ ወደ ሳጥን የላካትን ኳስ በመጨረሻ ንክኪው አቤል ሀብታሙ ጨርፏት መረብ ላይ አርፋ ጨዋታው በአሰልጣኝ ዘሪሁን ሸንገታው ኢትዮ ኤሌክትሪክ 1ለዐ አሸናፊነት ተቋጭቷል።

የሊጉ መሪን ሲዳማ ቡናን ከኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ያገናኘው መርሀግብር በሲዳማ ቡና 1ለ0 አሸናፊነት ተቋጭቷል። ዘጠኝ ሰዓት ይጀመራል በሚል ቀደም ብሎ ሰዓት የተያዘለት ይህ ጨዋታ ሲዳማ ቡናዎች ካስመዘገቡት ካሶቶኒ (ካልሲ) ውጪ ከንግድ ባንክ ጋር ተመሳሳይነት ስላለው በዕለቱ ዳኞች እንዲቀይሩ በመደረጉ ምክንያት ጨዋታው ለ21 ደቂቃዎች ዘግይቶ ለመጀመር ተገዷል። በመጀመሪያው አጋማሽ መደበኛው ደቂቃ ተጠናቆ በተሰጠው ጭማሪ 45+2 ላይ ከቅጣት ምት ተሻግሮ በግንባር ተጨርፎ የመጨረሻዋን ኳስ ያገኘው አቤል ያለው ወደ ጎልነት ቀይሮ ሲዳማን ቀዳሚ አድርጓል። ከዕረፍት መልስ የንግድ ባንኩ የግብ ዘብ ጊቤ ጆብ ኳስን ከግብ ክልል ውጪ ነክተሀል በሚል በዕለቱ ሁለተኛ ረዳት ዳኛ ሲራጅ ኑርበገን ጥቆማ በቀጥታ ቀይ ከሜዳ ከወጣ በኋላ ጨዋታው መቋጫውን አግኝቷል።

ሌላኛው አዲስ አበባ ላይ ሀድያ ሆሳዕናን ከኢትዮጵያ ቡና አገናኝቶ በነበረው ጨዋታ 25ኛው ደቂቃ ላይ ቡናማዎቹ ዘላለም አባተ ከአቡበከር አዳሙ የደረሰውን ኳስ የተከላዮች አለመናበብ ታክሎበት መሪ ቢያደርጋቸው 40ኛው ደቂቃ እዮብ አለማየሁ በግንባር ገጭቶ ባስቆጠራት ጎል ሀድያ ሆሳዕናዎች አቻ መሆን ችለዋል ነገር ግን ከሦስት ደቂቃዎች መልስ ፉዓድ ኢብራሂም ከቅጣት ምት አሻምቶ አምበሉ ራምኬል ጀምስ በግንባር ገጭቶ ኢትዮጵያ ቡናን ዳግም መሪ አድርጎ አጋማሹ ተገባዷል።

ጨዋታው ከዕረፍት ሲመለስ ጥሩ ፉክክርን እያሳየን ቀጥሎ 88ኛው ደቂቃ ግን ጎል አስመልክቶናል። የቀድሞው የቡናማዎቹ ተጫዋቾች እና ቡድኑን በተቃራኒው የገጠሙት ጫላ ተሺታ በማቀበሉ ብሩክ በየነ በማስቆጠሩ ተሳክቶለት ጨዋታው በመጨረሻም ሀድያ ሆሳዕና አቻ ሆኖ 2ለ2 ተፈፅሟል።

በሀዋሳ ዩኒቨርስቲ ስታዲየም አመሻሹን ቀዝቀዝ ባለው ዝናባማ አየር መከናወን የቻለው የወላይታ ድቻ እና ፋሲል ከነማ መርሀግብር ፋሲሎችን ባለ ድል አድርጎ ተጠናቋል። 21ኛው ደቂቃ ላይ ዳግም አወቀ ከቀኝ መስመር ያሻገረውን ኳስ ታምራት እያሱ በግንባር ገጭቶ ከመረብ ያሳረፋት ብቸኛ ግብ አፄዎቹ 1ለ0 አሸንፈው ወጥተዋል።

አስተያየት ይስጡ