7 ጎሎች እና ሁለት ድንቅ የቅጣት ምት ጎሎች በነበሯቸው ሁለት ጨዋታዎች ነገሌ አርሲ ድል ሲቀናው ሀዋሳ ከተማ እና ወልዋሎ ነጥብ ተጋርተዋል።

ሁለት ግሩም የቅጣት ምት ጎሎችን ባየንበት ጨዋታ ነገሌ አርሲ በጭማሪ ደቂቃ መደምደሚያ ላይ ሦስት ነጥብን ወደ ቋቱ ከቷል። ጥሩ ፉክክር ከታየበት የመጀመሪያው አጋማሽ በይበልጥ የጎል ሙከራዎችን ያየንበት ሁለተኛው አጋማሽ በጎል ፌሽታ የደመቁ ነበር። 51ኛው ደቂቃ ላይ በሳጥኑ ትይዩ መናፍ ዐወል በሀቢብ ከማል ላይ የሰራውን ጥፋት ተከትሎ የዕለቱ ኢንተርናሽናል ዋና ዳኛ ማኑሄ ወልደፃዲቅ የሰጡትን የቅጣት ምት ዳዊት ተፈራ የናትናኤል ተፈራ መረብ ላይ በግሩም አመታት በማሳረፍ ቡድኑን ቀዳሚ ቢያደርግም ከአሰልጣኝ ስንብት በኋላ በዳዊት ታደለ እና ዳዊት ሀብታሙ የሚመሩት አዳማ ከተማዎች 79ኛው ደቂቃ ላይ የአቻነት ጎልን አግኝተዋል።

ቢኒያም ፀጋዬ በሳጥኑ የቀኝ ክፍል ጠርዝ አብዱልከሪም መሐመድ ላይ በሰራው ጥፋት የተገኘን የቅጣት ምት ዳዋ ሆቴሳ በቀጥታ መቶ ጎል በማድረግ በዓመቱ የመጀመሪያ ጎሉን ማስቆጠር ችሏል። ጨዋታው ቀጥሎ ወደ መጨረሻዎቹ ደቂቃዎች አንዳች ነገርን ለመፍጠር ጥረት ያደረጉት ነገሌ አርሲዎች በተሰጠው የጭማሪ ስድስት ደቂቃዎች ውስጥ ማሳረጊያው ላይ ከማዕዘን ምት ዳዊት ተፈራ ሲያሻማ የአዳማ ተከላካዮች የተጫዋች አያያዝ ስህተት ታክሎ ቁመታሙ ርሆቦት ሰላሎ በግንባር ገጭቶ በማስቆጠር ወርቃማ ሦስት ነጥብን ለሰጎኖቹ በማስገኘት 2ለ1 በሆነ ውጤት ተቋጭቷል።
ሀዋሳ ላይ ሀዋሳ ከተማ ወደ ሊጉ መሪ በይበልጥ የሚጠጋበትን ዕድል ሳይጠቀምበት ቀርቷል። በመጀመሪያው አጋማሽ ጥሩ ለመንቀሳቀስ ጥረት ያደረጉት እና የተሻለውን ጊዜ ያሳለፉት ሀዋሳዎች ጎል ያስቆጠሩት 29ኛው ደቂቃ ላይ ነበር። የአብስራ ደግፌ ከቀኝ የራሱ ሜዳ በረጅሙ ከተከላካይ ጀርባ የጣለውን ኳስ ያሬድ ብሩክ የግል ጥረቱን አክሎ በሊጉ ስድስተኛ ጎሉን በማስቆጠር ሐይቆቹን መሪ ማድረግ ችሏል። ከዕረፍት መልስ በይበልጥ ግለቱ ከፍ ብሎ በታየው የቡድኖቹ ጨዋታ ሊጠናቀቅ በተቃረበባቸው ደቂቃዎች ሦስት ጎሎችን ተመልክተናል።

86ኛው ደቂቃ ላይ ለማጥቃት ቅድሚያ ሰጥተው በአጋማሹ የታዩት ቢጫዎቹ ሙሉአለም መስፍን ከቅጣት ምት ሲያሻማ ኮንኮኒ ሀፊዝ በግንባር ገጭቶ የሰጠውን ነፃ ሆኖ ኳሷን ያገኘው ነፃነት ገብረመድኅን የአቻነት ግብን መረቡ ላይ አስቀምጧል። ጎል ካስቆጠሩ በኋላ በይበልጥ መነቃቃት የጀመሩት ወልዋሎዎች በተጨመረው አምስት ደቂቃ ውስጥ ተቀይሮ የገባው አፈወርቅ ሐይሉ 90+2ኛው ደቂቃ በረጅሙ ከተከላካይ ጀርባ የጣለውን ኳስ ብሩክ ታደለን አልፋ ዳዊት ገብሩ አግኝቷት የሰይድ ሀብታሙ ከግቡን መውጣት አይቶ ተጫዋቹ መሪ ያደረጋቸውን ጎል አስቆጥሯል።
ጨዋታው በዚህ የሚያልቅ ቢመስልም ከሁለት ደቂቃዎች መልስ ሽመልስ በቀለ ከቅጣት ምት የግብ ዘቡ ናትናኤል ኪዳኔ ጉልህ ስህተት ታክልበት ጎል በማስቆጠር ጨዋታው በመጨረሻም 2ለ2 ተደምድሟል። በጨዋታው ሀዋሳዎች የፍፁም ቅጣት ምት አጋጣሚን አግኝተው የዕለቱ ዳኛ ኤፍሬም ደበሌ ስህተት እና የወልዋሎው ግብ ጠባቂ ናትናኤል ኪዳኔ በእርሱ ስህተት ከቅጣት ምት በተቆጠረችው ጎል በእንባ ከሜዳ የወጣበት ክስተት ተጠቃሾቹ አጋጣሚዎች ነበሩ።
አስተያየት ይስጡ