ሀዋሳ ከተማ የሊጉን መሪ መከተሉን ሲቀጥል አርባምንጭ ከተማ ነጥቡን ያሳደገበትን ጣፋጭ ውጤት አግኝቷል።
በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ስታዲየም ላይ ከመሪው ሲዳማ ቡና ዝቅ ብሎ የተቀመጠው ሀዋሳ ከተማን ከመቐለ 70 እንደርታ ጋር ያደረገውን ጨዋታ ሐይቆቹን አሸናፊ በማድረግ ተቋጭቷል። መቐለዎች ሻል ያለውን ጊዜ ቢያሳልፉም በሁለተኛው አጋማሽ ውጤቱን አጥብቀው የሚፈልጉት ሐይቆቹ ጎል አስቆጥረዋል። 74ኛው ደቂቃ ላይ ከቀኝ መስመር አቅጣጫ አዲሱ ፈራሚ አድናን ረሻድ በረጅሙ ወደ ሳጥን ከተከላካይ ጀርባ የጣላትን ኳስ በአሰጋኸኝ ጴጥሮስ ተጨርፋ ኳሷን ያገኘው ሽመልስ በቀለ ከጠባብ ቦታ ላይ ያስቆጠራት ብቸኛ ጎል ሀዋሳ ከተማ 1ለ0 በሆነ ውጤት አሸናፊ መሆን እንዲችል አድርጓል። ሀዋሳም ከመሪው ሲዳማ ቡና በሁለት ነጥብ ዝቅ ብሎ እግር በእግር መከተሉን ቀጥሏል።
ሀዋሳ ዩኒቨርስቲ ሜዳ ላይ ደግሞ አዳማ ከተማን ከአርባምንጭ ከተማ ጋር ባገናኘው መርሀግብር አዞዎቹ 2ለ0 በሆነ ረተዋል። አርባምንጭ ከተማዎች በተሻለ የሜዳ ላይ ፍላጎት በተንቀሳቀሱበት ጨዋታ 27ኛው ደቂቃ ላይ የአዳማ ከተማው የግብ ዘብ አላዛር ማርቆስ የተሳሳተው ኳስ አሸናፊ ተገኝ በአግባቡ ተቆጣጥሮ ያመቻቸለትን ናይጄሪያዊው አጥቂ ጄሮም ፊሊፕ መረቡ ላይ አሳርፏታል።
ከዕረፍት መልስም ከአዳማ ከተማ በተሻለ ንቃት መጫወታቸውን የቀጠሉት አርባምንጭ ከተማዎች 62ኛው ደቂቃ ሌላ ጎል አስቆጥረው ድላቸውን አረጋግጠዋል። አሸናፊ ተገኝን ተክቶ ወደ ሜዳ የገባው እና በዝውውር መቋጨው ቀን አዞዎቹን የተቀላቀለው ጋናዊው አጥቂ መሐመድ አብዱራህማን በመጀመሪያ የሊግ ጨዋታው ከፍቆር ግዛው ያገኛኝን ኳስ በመጀመሪያ ንክኪው በአስደናቂ መልኩ ተከላካዮችን እና የግብ ዘቡን አላዛርን ጭምር በማለፍ ግሩም ጎልን በማስቆጠር ክለቡ አሸናፊ ሆኗል። ቡድኑም በሊጉ ለመክረም መጣጣሩን ቀጥሏል።
አስተያየት ይስጡ