በ2014 የቤትኪንግ ኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ በተለይም በመጀመሪያ ዘጠኝ ሳምንታት ላይ በከፍተኛ የውጤት ቀውስ ውሰጥ ገብቶ በሊጉ የደረጃ ሰንጠረዥ ግርጌ ላይ ለበርካታ ሳምንታት ተቀምጦ የቆየው ጅማ አባጅፋር ከ10ኛ ሳምንት በኋላ ድሬዳዋ ላይ በተደረጉ ጨዋታዎች ጥሩ መነቃቃት በማሳየት ነጥቦችን መሰብሰቡ ይታወቃል ።
በሊጉ ለመተረፍ በቀጣይ ጨዋታዎች ላይ ነጥቦችን መሰብሰብ የግድ የሚለው ክለቡም በተከፈተው የዝውውር መስኮት ላይ ተጫዋቾችን ወደ ቡድኑ ለመቀላቀል እንቅስቃሴ ሲያደርግ የቆየ ሲሆን ዛሬ በተሰማው መረጃ ደግሞ በክረምቱ ካስፈረማቸው ሶሰት ተጫዋቾች ጋር በስምምነት ተለያይቷል ።
የመጀመሪያው የግራ መስመር ተከላካዩ አስናቀ ሞገስ ሲሆን የአሰልጣኝ አሸናፊ በቀለን ቡድን ከመቀላቀሉ በፊት በደደቢት ፤ ኢትዮጵያ ቡና ፤ ባህርዳር ከተማ እና መቐለ 70 እንደርታ ተጫውቶ ማሳለፉ የሚታወስ ሲሆን ሁለተኛው ተጫዋች ደግሞ ከአስናቀ ጋር በተመሳሳይ ቦታ ላይ የሚጫወተው እና ጅማ አባጅፋርን ከመቀላቀሉ በፊት በቅዱስ ጊዮርጊስ እና ባህርዳር ከተማ ተጫውቶ ያሳለፈው ሚኪያስ ግርማ ነው ። ከዚህ ቀደም በኢትዮ ኤሌክትሪክ ፤ ሜታ ቢራ ፤ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ፤ ሀዋሳ ከተማ ፤ ኢትዮጵያ ቡና እና በድጋሚ በኢትዮ ኤሌክትሪክ የግብ ዘብ ሆኖ ካገለገለ በኋላ ወደ ጅማ አባጅፋር አምርቶ የነበረው ዮሀንስ በዛብህ ሶስተኛው ከክለቡ ጋር የተለያየው ተጫዋች ነው ።
ጅማ አባጅፋር የሁለተኛ ዙር የመጀመሪያ ጨዋታውን በነገው ዕለት ከምሽቱ 12 ሰዓት ላይ በሊጉ የደረጃ ሰንጠረዥ 4ኛ ላይ ከሚገኘው ሀዋሳ ከተማ ጋር የሚያደርግ ይሆናል ።
አስተያየት ይስጡ