“ኢትዮጵያ ቡና ለፍቶ ጥሮ እንጂ ከኮብል ስቶን ተቀንሶ የሚሰጠው ክለብ አይደለም”
አቶ ገዛኧኝ ወልዴ
/የኢት.ቡና ዋና ስራ አስኪያጅ/
“የቤት መግዢያ እንጂ የቤት እጥረት አለ ብለን አናምንም”
አቶ ወሰንሰገድ አሰፋ
/ የኪ ሃውሲንግ የህዝብ ግንኙነት ሃላፊ /
ኪ ሀውሲንግ ፋይናንስ ሶሉሽን ግንቦት 11/2016 ይካሄዳል ለተባለው ለ7ኛው የኢትዮጵያ ቡና የቤተሰብ ሩጫ በፕላቲኒየም ደረጃ በ2 ሚሊዮን ብር ስፖንሰር ማድረጉ ይፋ ሆነ።
- ማሰታውቂያ -
ዛሬ ከቀትር በኋላ በካሌብ ሆቴል በተሰጠው መግለጫ ላይ ለኢ.ት ቡና አመታዊ ሩጫ ኪ ሀውሲንግ ሶሉሽን በፕላቲኒየም ደረጃ ግንቦት 11/2016 የሚካሄደውን የሩጫ ውድድርን ስፖንሰር ከማድረጉም በተጨማሪ ክለቡና ደጋፊው የሚጠቀሙበትን እቅዱንም ይፋ አድርጓል።
የተቋሙ የህዝብ ግንኙነት ሃላፊ አቶ ወሰንሰገድ አሰፋ እንደተናገሩት ” በሚሊዮን የሚቆጠር ደጋፊ ካለው ኢትዮጵያዊ ቡና ጋር በጋራ ለመስራት ስንወስን የጋራ ጥቅም እንዳለው አረጋግጠን ነው” ሲሉ ተናግረዋል።
አቶ ወሰን ሰገድ እንደተናገሩት “በ10 አመት 100 ሺሀ ሰዎች ቤት እንዲያገኙ እየሰራን ነው በዚህ መሰረት 1 የቡና ደጋፊ ኪ ሀውሲንግ ሶሉሽን ሄዶ ቢመዘገብ ክለቡ 4ሺህ ብር …10 ሺህ የቡና ደጋፊ ቢመዘገብ ደግሞ ክለቡ 400 ሚሊዮን ብር …እንዲሁም 250 ሺህ ደጋፊ ቢመዘገብ ኢትዮጵያ ቡና 1 ቢሊዮን ብር ያገኛል በእኛ ግምገማ የቤት መግዢያ እንጂ የቤት እጥረት አለ ብለን አናምንም” ሲሉ ተቋማቸው ለኢትዮጵያ ቡና ይዞ የመጣውን እቅድ አሳውቀዋል።
“ቤት የማይፈልግ የለም ደጋፊው ኪ ሃውሲንግ ፋይናንስ ሶሉሽን ሄዶ 83 ሺህ ብር ከፍሎ ቢመዘገብ የሚወደው ክለቡ 4 ሺህ ብር ያገኛል። ደጋፊው ብሩ እንደማይበላ ከቡና ባንክና ከቡና ኢንሹራንስ ማረጋገጫውን ያገኛል እስከ ሰኔ 30/2016 ድረስ 5ሺህ ደጋፊ ቢመዘገብ ክለባችን 20 ሚሊዮን ብር ያገኛል ይሄ ደግሞ የ2017 ቡድናችንን እንድንገነባ ያግዘናል” ያሉት የኢትዮጵያ ቡና ዋና ስራ አስኪያጅ አቶ ገዛኧኝ ወልዴ ” እግርኳሳችን ተፎካካሪነትን በእኩል አያሳይም አንዱ ክለብ 250 ይመደብለታል እኛ ደግሞ ቆፍረን 100 ሚሊዮን ብር አካባቢ እናገኛለን ይሄ እኩል ተፎካካሪነትን አይፈጥርም
ኢትዮጵያ ቡና ለፍቶ ጥሮ እንጂ ከኮብል ስቶን ተቀንሶ የሚሰጠው ክለብ አይደለም” ሲሉ አቶ ገዛኧኝ ክለቡ የተለያየ የገቢ ምንጮችን ለማግኘት ተግቶ እንደሚሰራ አረጋግጠዋል።