* በአስራ ዘጠነኛው ሳምንት የመጀመሪያ መርሐግብር መቻል በምንይሉ ወንድሙ ብቸኛ ግብ ወላይታ ዲቻን 1ለ0 በሆነ ዉጤት ማሸነፍ ችሏል።
በትላንትናው ዕለት በድንገት ህይወቱ ላለፈዉ የባህርዳር ከተማ እና የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ተጫዋች አለልኝ አዘነ የአንድ ደቂቃ የህሊና ፀሎት በማድረግ በኢንተርናሽናል ዋና ዳኛ ዶ/ር ሀይለየሱስ ባዘዘዉ መሪነት ቀን አስር ሰዓት ሲል በጀመረዉ ጨዋታ በወቅቱ በጣለዉ ዝናብ ምክንያት ሜዳዉ ያን ያህል በምቾት ኳስ ለመጫወት አመቺ ስላልነበረ ሁለቱም ክለቦች ይህ ነዉ የሚባል ተጠቃሽ ሙከራ እምብዛም ሊያስመለክቱን አልቻሉም ።
በዚህ ሂደት መከናወን በቀጠለዉ ጨዋታ በግማሽ ሰዓት ላይ መቻሎች መሪ መሆን የቻሉበትን ግብ አግኝተዋል ። በዚህም ከኋላ ክፍል የተጣለዉን ኳስ ሽመልስ በቀለ ተቆጣጥሮ ሳጥን ውስጥ በመግባት ለምንይሉ ሲያቀብለዉ አጥቂዉ ኳሷን ወደ ግብነት በመቀየር ክለቡን መሪ ማድረግ ችሏል።
- ማሰታውቂያ -
እረፍት በፊት ከነበረዉ በተወሰነ መልኩ ሙከራዎችን ባስመለከተን ሁለተኛዉ አጋማሽም መሪዎቹ መቻሎች በሽመልስ በቀለ እና በግብ አስቆጣሪዉ ምንይሉ ወንድሙ አማካኝነት ሙከራዎችን ማድረግ ችለዉ የነበረ ቢሆንም የግብ ዘቡ ቢኒያም ገነቱ ሙከራዎቹን ተቆጣጥሯል።
በ63ተኛዉ ደቂቃ ላይ ዳግም ጥሩ የግብ ዕድል አግኝተዉ በምንይሉ አማካኝነት ሙከራ ማድረግ ችለዉ የነበሩት መቻሎች በይበልጥ በኳስ ቁጥጥር ላይ ትኩረት አድርገዉ ለመንቀሳቀስ ሲሞክሩ ተስተውሏል። በተደጋጋሚ በሚጥሏቸዉ ረጃጅም ኳሶች አንዳች ነገርን ለመፍጠር ሲጥሩ የነበሩት ዲቻዎች በ72ተኛዉ ደቂቃ ላይ በአበባየሁ አጂሶ አማካኝነት ሙከራ ቢያደርጉም ግብ ጠባቂዉ ኤልዌንዚ ተቆጣጥሯታል።
በሁሉም ረገድ የተቀዛቀዘ የጨዋታ እንቅስቃሴ ባስመለከተን የቀኑ ጨዋታም በመጨረሻው ደቂቃ ላይ ወላይታ ዲቻ በእዮብ ተስፋየ አማካኝነት አስደናቂ ሙከራ አድርገዉ የነበረ ቢሆንም ኳሷ የግቡን ቋሚ ነክታ ወደ ዉጭ ወጥታለች ፤ በዚህም የሁለቱ ክለቦች የመጀመሪያ 19ነኛ ሳምንት ጨዋታ በመቻል 1ለ0 አሸናፊነት ተጠናቋል።
* በምሽቱ ሁለተኛ መርሐግብር ኢትዮጵያ ቡና እና ፉሲል ከነማ መርሐግብራቸዉን በአቻ ዉጤት አገባደዋል።
በኢንተርናሽናል ዋና ዳኛ በላይ ታደሰ መሪነት ምሽት ላይ በጀመረዉ የሳምንቱ ታላቅ ጨዋታ በመጀመሪያዎቹ ደቂቃዎች ላይ ሁለቱም ክለቦች ተመጣጣኝ የሚባል የጨዋታ እንቅሰቃሴ ያስመለከቱን ሲሆን ፤ ክፍት በነበረዉ ጨዋታም በሁለቱም በኩል ተደጋጋሚ ሙከራዎችን ለመመልከት ችለናል።
በዚህም በ15ተኛዉ ደቂቃ ላይ የመጀመሪያ ሙከራ አማኑኤል ገ/ሚካኤል ከግራ በኩል ከአቤል እንዳለ የተቀበለዉን ወደ ግብ ሞክሮ የነበረ ቢሆንም ኳሷ ግን በአናት ላይ ወጥታለች። በዚህ ሂደት ጅማሮዉን ባደረገዉ መርሐግብሩ በ20ኛዉ ደቂቃ ላይ የግብ ዘቡ በረከት አማረ እና አማኑኤል ገ/ሚካኤል እርስ በእርስ ተጋጭተዉ ጉዳት አጋጥሟቸዉ ከሜዳ ወጥተዋል።
በሂደት እየተጋጋለ በቀጠለዉ ጨዋታ ቡናማዎቹ በበፍቃዱ አማካኝነት ድንቅ ሙከራ ከሳጥን ውጭ አድርገዉ የነበረ ቢሆኖንም ኳሷ በግቡ ቋሚ ለጥቂት ወጥታለች። በዚህ ሂደት በቀጠለዉ ጨዋታም በ31ኛዉ ደቂቃ ላይ ተቀይሮ የገባዉ ናትናኤል ገ/ጊዮርጊስ ያቀበለዉን ኳስ አቤል እንዳለ በቀላሉ ወደ ግብነት ቀይሮ አፄዎቹን መሪ አድርጓል።
ከግቧ መቆጠር በኋላ በተደጋጋሚ የግብ ዕድሎችን ለመፍጠር ሲጥሩ የተስተዋሉት ቡናማዎቹ አብዱል ከሪም ያቆመለትን ኳስ መስፍን በቀጥታ ወደ ግብ ሲመታ ሳማኪ በድንቅ ብቃት ሲመልስ ዳግም የተገኘዉን ኳስ በፍቃዱ ሞክሮ የነበረ ቢሆንም ኳሷ በግቡ ቋሚ ለጥቂት ወጥታለች።
በዚህ ሂደት በቀጠለዉ ጨዋታም አጋማሹ ሊጠናቀቅ ሲል መስፍን ታፈሰ ከአብዱል ከሪም የተቀበለዉን ኳስ ከተከላካዮች ጋር ታግሎ ወደ ግብነት በመቀየር ክለቡን አቻ አድርጎ አጋማሹ ተጠናቋል። በሁለተኛዉ አጋማሽ በመጠኑም ቢሆን ብልጫ የተወሰደባቸዉ ቡናማዎቹ በ58ተኛዉ ደቂቃ ላይ በአብዱልከሪም አማካኝነት እና ከአንድ ደቂቃ በኋላ ደግሞ መስፍን ታፈሰ ከዚሁ ተጫዋች በተቀበለዉ ኳስ ድንቅ ሙከራ ማድረግ ችለዋል።
በጥሩ ፉክክር በቀጠለዉ ጨዋታ በ78ተኛዉ ደቂቃ ላይ ዳግም ቡናማዎቹ በተከላካዩ ዋሳዋ ጂኦፍሪ አማካኝነት ከርቀት ድንቅ ሙከራ ቢያደርጉም የግብ ዘቡ ሳማኪ ኳሷን አውጥቷታል። በተደጋጋሚ በግራ በኩል በኢትዮጵያ ቡናዉ የመስመር አጥቂ መስፍን ታፈሰ እንቅስቃሴ ተቸግረዉ የነበሩት እና እየተቀዛቀዙ የሄዱት አፄዎቹ በጨዋታው መገባደጃ ወቅት በ83ተኛዉ ደቂቃ ላይ በሽመክት ጉግሳ አማካኝነት ድንቅ ሙከራ ቢያደርጉም ኳሷ የግቡን ቋሚ ነክታ ወደ ዉጭ ወጥታለች። የሳምንቱ ታላቅ መርሐግብርም አንድ አቻ በሆነ ዉጤት ተጠናቋል።