በቤትኪንግ ኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ23ተኛ ሳምንት የመጀመሪያ ዕለት ቀን ጨዋታ ወላይታ ዲቻ እና አዳማ ከተማ ጨዋታቸውን አንድ አቻ በሆነ ውጤት አገባደዋል።
በተመሳሳይ ባለፉት ሁለት ጨዋታዎች ተከታታይ ድል አስመዝግበዉ ለዛሬዉ ጨዋታ የመጡት ሁለቱም ክለቦች በተለይ አዳማ ከተማ በንፅፅር የኳስ ቁጥጥር የበላይነቱን በመውሰድ ከሚገኙ ዕድሎች ግብ ለማስቆጠር ሲጥር በተቃራኒው የአሰልጣኝ ፀጋየ ኪዳነማርያሙ ቡድን ወላይታ ዲቻ ደግሞ በጥብቅ መከላከል አልፎ አልፎ በሚገኙ የመልሶ ማጥቃት እንቅስቃሴዎች ግብ ለማስቆጠር ሲጥሩ ተስተውሏል።
በሙከራ ረገድ እምብዛም በነበረዉ የዕለቱ ጨዋታ በመጀመሪያው አጋማሽ ከተደረጉ ተጠቃሽ እንድ ሁለት ሙከራዎች መካከል የአዳማ ከተማዉ የፊት መስመር ተጫዋች ዮሴፍ ታረቀኝ እጅግ ጥሩ የሚባል የግብ ዕድልን መፍጠር ችሎ የነበረ ሲሆን ፤ ከዚች እንቅስቃሴ በኋላ በድጋሚ አድናን ረሻድ ከአሜ መሐመድ የተቀበለዉን ኳስ ወደ ግብ ሞክሮ የነበረ ቢሆንም ግብ ጠባቂዉ ቢኒያም እንደምንም ኳሷን አምክኖበታል።
- ማሰታውቂያ -
በተቃራኒው በጠጣር የመከላከል አደረጃጀት በርከት ያሉ ደቂቃዎችን ሲያሳልፉ የነበሩት ዲቻዎ በአጋማሹ ምንም እንኳን ያን ያህል አደገኛ የሚባል የግብ ዕድል መፍጠር ባይችሉም በፊት መስመር አጥቂዉ ስንታየሁ መንግስቱ እና ቃልኪዳን ዘላለም እንዲሁም አማካኝነት ጥሩ ጥሩ ሙከራዎችን ማድረግ ቢችሉም በመጀመሪያው አጋማሽ ግን ሁለቱም ቡድኖች ግብ ማስቆጠር ሳይችሉ ለዕረፍት ወደ መልበሻ ክፍል አምርተዋል።
ከዕረፍት መልስ በንፅፅር ጥሩ የሚባል የጨዋታ እንቅስቃሴ መመልከት የቻልን ቢሆንም በሙከራ ረገድ ግን ሁለቱም ቡድኖች አይናፋር ሁነዉ ተስተውሏል። በተለይ የአዳማዉ የግራ ተመላላሽ ደስታ ዮሐንስ እና የዲቻዉ አጥቂ ስንታየሁ አጋማሹ እንደተጀመረ አካባቢ ያመከኗቸዉ ኳሶች በሁለቱም ክለበች በኩል ወደ ግብነት ቢቀየሩ ምናልባት የጨዋታውን እንቅስቃሴ ሊቀይር የሚችልበት አጋጣሚ ነበር ማለት ይቻላል።
በዚህ ሂደት በቀጠለዉ የሁለቱ ክለቦች ጨዋታም በ65ተኛዉ ደቂቃ ላይ ግብ ተስተናግዶበታል ፤ በዚህም በዕለቱ ድንቅ ሲንቀሳቀስ የነበረዉ የሴፍ ታረቀኝ የግል ብቃቱን ተጠቅሞ እና ከሌላኛዉ የቡድን አጋሩ አሜ መሐመድ ጋር በአንድ ንክኪ ኳሷን ወደ ግብነት በመቀየር ክለቡን መሪ ማድረግ ችሏል።
ከዚች ግብ መቆጠር በኋላ ተቀዛቅዞ በቀጠለዉ የሁለቱ ክለቦች ጨዋታም በ81ኛዉ ደቂቃ ላይ ዲቻዎች አቻ መሆን የቻሉበትን ግብ ማስቆጠር ችለዋል። በዚህም ከዲቻ የቀኝ ማጥቃት በኩል የተሻገረለትን ኳስ ቢኒያም ፍቅሩ የግል ብቃቱን ተጠቅሞ ወደ ግብነት በመቀየር ክለቡን አቻ ማድረግ ችሏል። ከዲቻዎች የአቻነት ግብ አስቀድሞም አንጋፋዉ የተከላካይ ስፍራ ተጫዋች ደጉ ደበበ በሁለተኛ ቢጫ በቀይ ካርድ ከሜዳ የተሰናበተ ሲሆን ጨዋታውም ተጨማሪ ግብ ሳይስተናገድበት አንድ አቻ በሆነ ዉጤት ተጠናቋል።