በኬኒያ ናይሮቢ ሲካሄድ በሰነበተው የምስራቅና የመካከለኛው አፍሪካ ክለቦች ሻምፒዮና (ሴካፋ) የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የሴቶች እግር ኳስ ቡድን በኬኒያዉ አቻው ቪጋ ክዊንስ ተሸንፎ 2ተኛ ደረጃን ይዞ አጠናቋል፡፡
በዚሁ መሠረት ዛሬ ከቀኑ 10፡00 የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የሴቶች እግር ኳስ ቡድን ከኬኒያው ቬጋ ኩዊንስ ጋር ባደረገው የፍጻሜ ጨዋታ 2ለ1 በሆነ ውጤት በመሸነፉ የነበረውን የሻፒዮናነት ዕድል አጥቷል፡፡ እስከ መደበኛው ሰዓት አንድ አቻ የነበሩት ቡድኖቹ፣ በተጨማሪ ደቂቃ በተሰጠ የፍፁም ቅጣት ምት ጎል ቪጋ ክዊንስ አሸናፊ ሆኖአል።
በዚህም ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የብር ሜዳሊያ እና የ20 ሺህ ዶላር ተሸላሚ ሲሆን ፤ በዛሬው ጨዋታ ሁለት ጎሎችን አስቆጥራ ቡድኗን የዋንጫ ባለቤት ያደረገችው ጄንትሪክስ ቺካንጋዋ የውድድሩ ኮከብ ተጫዋች ተብላ ስትሸለም የንግድ ባንክ ተጫዋች የሆነችው ሎዛ አበራ ደግሞ በ13 ጎሎች የውድድሩ ኮከብ ጎል አግቢ ሆናለች፡፡
በፍፃሜው ጨዋታም ትላልቅ ሀላፊዎች እና የስፖርቱ አመራሮች በስታዲየም የተገኙ ሲሆን በተጨማሪም የፊፋ ዋና ፀሀፊዋ ፋጡማ ሳሞራ ከጨዋታዉ መጠናቀቅ በኋላ ለኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ክለብ የድጋፍ መልዕክታቸውን አስተላልፈዋል። ” የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ክለብ ችሎታችሁን እና ፍቅራችሁን ማድነቅ እፈልጋለሁ ፣ ራሳችሁን ቀና በማድረግ ልትኮሩ ይገባል” ሲሉ ተደምጠዋል።
ቪጋ ክዊንስ ምስራቅ አፍሪካን በመወከል በግብፅ ለሚካሄደው የአፍሪካ ሻምፒዮንስ ሊግ ተሳታፊ የሚሆኑ ይሆናል። በተያያዘም ለደረጃ በተደረገ ጨዋታ የኡጋንዳው ሌዲ ዶቭስ የታንዛኒያውን ሲምባ ኩዊንስ 2 ለ 1 በማሸነፍ ሻምፒዮናውን በሶስተኛ ደረጃ አጠናቋል፡፡
አስተያየት ይስጡ