በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 10ኛ ሳምንት ጨዋታ በወልቂጤ ስታዲየም ድሬዳዋ ከተማን ያስተናገደው ወልቂጤ ከተማ ሳዲቅ ሴቾ በመጀመሪያው አጋማሽ ባስቆጠራት ብቸኛ ግብ ማሸነፍ ችሏል።
በደጋፊዎች ደማቅ ድጋፍ የተካሄደው የሁለቱ ቡድኖች ጨዋታ ሞቅ ብሎ ነው የተጀመረው። ፈጣን እንቅሰቃሴ የታየበት ጨዋታ የመጀመሪያውን ሙከራ ለማግኘት 11ደቂቃዎች ነበር የፈጀበት። 11ኛው ደቂቃ ላይ የወልቂጤ ከተማው ጫላ ተሺታ በግሩም ሁኔታ በግንባሩ የገጨው ኳስ የግቡ አግዳሚ ገጭቶበታል። ከዚህች ሙከራ በኋላ በሁለቱም ቡድኖች በኩል ፈጣን ጨዋታ ለመጫወት ጥረት አድርገዋል። ይህንንም ተከትሎ 23ኛው ደቂቃ ላይ ከአህመድ ሁሴን የተቀበለውን ኳስ ጫላ ተሺታ በግሩም ሁኔታ አስቆጥሮ ክትፎዎቹን ቀዳሚ ማድረግ ችሏል።
- ማሰታውቂያ -
ከግቡ መቆጠር በኋላ አፈግፍገው ሲጫወቱ የነበሩት ድሬዎች ወልቂጤ ከተማዎችን ተጭነው ለመጫወት ሲሞክሩ ታይተዋል። 25ኛው ደቂቃ ላይ የድሬዳዋ ከተማው ሪችሞንድ ኦዶንግ እንዲሁም 27ኛው ደቂቃ ላይ ዋለልኝ ገብሬ የሞከሯቸው ኳሶች ተጠቃሽ ናቸው። 30ኛው ደቂቃ ላይ ጫላ ተሺታ የሞከረው ኳስ በግቡ አናት ላይ ወጥቶበታል። ከዚህ በኋላ ይህ ነው የሚባል ሙከራ ሳይስተዋልበት የመጀመሪያው አጋማሽ ተጠናቋል።
በሁለተኛው አጋማሽ ሁለቱም ቡድኖች ግብ ለማግኘት ሙከራ አድርገዋል። 55ኛው ደቂቃ ላይ በወልቂጤ የግብ ክልል አካባቢ የተገኘውን ቅጣት ምት የድሬዳዋ ከተማው ኤልያስ ማሞ መቶት ወደ ውጭ ወጥቷል። ከዚህ ሙከራ 4ደቂቃዎች በኋላ 59ኛው ደቂቃ ላይ የወልቂጤ ከተማው አዳነ ግርማ የመታውን ቅጣት ምት የድሬዳዋ ከተማው ግብ ጠባቂ ቢተፋውም በአካባቢው ማንም ባለመኖሩ ወልቂጤ ከተማዎች ሳይጠቀሙበት ቀርተዋል።
ውጤቱንም ተከትሎ ድል ያደረጉት ወልቂጤ ከተማዎች በ11 ነጥቦች እና በ3የግብ እዳ 14ኛ ደረጃ ላይ ሲቀመጡ ተጋጣሚያቸው ድሬዳዋ ከተማ በአንፃሩ በ10ነጥቦች እና በ10የግብ እዳ 15ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጠዋል።