በአፍሪካ የክለቦች ሻምፒዮና ላይ ብቸኛ የሀገሪቱ ወኪል ሆኖ በመሳተፍ ላይ የሚገኘው ጅማ አባ ጅፋር ከሞሮኮው ሀሳኒያ አጋዲር ጋር የመልስ ጨዋታውን ነገ (ቅዳሜ) ምሽት 2ሰዓት በአጋዲር ከተማ ከ45ሺ ተመልካች በላይ በሚያስተናግደው ሌ ግራንድ ስታዲየም ያደርጋል።
ሁለቱ ቡድኖች የቶታል ካፍ የኮንፌዴሬሽን ዋንጫ ጨዋታቸውን ከሳምንት በፊት በአዲስ አበባ ስታዲየም አድርገው የአምናው የፕርምዬር ሊጉ አሸናፊ ጅማ አባጅፋር በሀገሩና በደጋፊው ፊት 1ለ0 በሆነ ውጤት መሸነፉ የሚዘነጋ አይደለም።
ካፍ ባወጣው መርሀ ግብር መሠረት የመልስ ጨዋታቸውን ነገ የሚያደርጉ ሲሆን ጅማ አባጅፋሮች ለጨዋታው ባለፈው ሐሙስ ምሽት ወደ ሞሮኮ ተጉዘዋል። ቡዱኑም
የጅማ አባጅፋር ቡድን ሐሙስ ምሽት ወደ ውድድሩ ስፍራ ሲጓዝ 15 ተጫዋቾችና 1 አሠልጣኝ ብቻ ይዞ መጓዙ ብዙዎችን ያነጋገረ ሲሆን የቡድኑ ምክትል አሠልጣኝና የግብ ጠባቂዎች አሠልጣኞች አብረው ሳይጓዙ በአንድ አሠልጣኝ ብቻ መጓዛቸው በርካቶች የተለያዩ ጥያቄዎችን እንዲያነሱ እያስገደዳቸው ነው።
በዚህ በኩል በተለይ ጨዋታው ወደ ቀጣዩ ዙር ለማለፍና ውጤቱን ለመቀልበስ ካለው ወሳኝነትና ፋይዳ አንፃር 15 ተጫዋቾች ብቻና ያለ ረዳትና የግብ ጠባቂዎች አሠልጣኝ በአንድ አሠልጣኝ ብቻ መጓዙ በውጤቱ ላይ አሉታዊ አስተዋጽኦ እንዳያሳድር በሚል ከወዲሁ ስጋታቸውን እየገለፁ ነው።
ጅማ አባጅፋር ወደ ሰፍራ ሲጓዝ አብረው ካልተጓዙት ከረዳቱና ከግብ ጠባቂዎች አሠልጣኝ ውጪ የቡድኑ የቴክኒክ ዳይሬክተር የሆኑት በርካታ ክለቦችን በማሰልጠንና ውጤታማ በመሆን የሚታወቁት አሠልጣኝ ወርቁ ደርገባም አብረው አለመጓዛቸውንም ነው የሀትሪክ የመረጃ ምንጮች የጠቆሙት።
በባንኮች፣በኢት.ቡና፣በብ/ቡድን አሠልጣኝነት የሚታወቁት የውጤትና የልምድ ባለቤት የሆኑት አሠልጣኝ ወርቁ ደርገባ ከጉዞው ውጪ ከመሆናቸው በፊት አብረው እንዲጓዙ ተጠይቀው”ተጫዋቾች ቀርተው እኔ ከምሄድ ቡድኑን የሚጠቅሙ ተጫዋቾች በእኔ ምትክ ይሂዱ”ማለታቸው በተጫዋቾችና በክለቡ የበላይ ሀላፊዎችና በደጋፊዎቹ አድናቆትና ከበሬታን ያተረፈላቸው ሲሆን በእሳቸው ምትክም አንድ ተጨማሪ ተጫዋች እንዲሄድ ምክንያት መሆናቸው ነው የተሰማው።
ኢትዮጵያን ወክሎ በቶታል የካፍ ቻምፒዮንስ ሊግ ተሳታፊ የሆነው ጅማ አባጅፋር ነገ ምሽት በአጋዲር ከተማ የሞሮኮውን ሀሳኒያ አጋዲርን ሲገጥም ጨዋታውን እንዲመሩ ሶስቱም ዳኞች ከአልጄሪያ መመደባቸውን የውድድሩ የበላይ አካል የሆነው ካፍ አሳውቋል።
አስተያየት ይስጡ