በይስሐቅ በላይ
ሌላው ልብ የሚሰብር አሳዛኝ ዜና፤ በኢትዮጵያ እግር ኳስ በተጨዋችነትና በአሰልጣኝነት ደማቅ አሻራውን ያሳረፈውና ታላቅ ውለታን ከዋሉ አሰልጣኞች አንዱ የሆነው ወንድማገኝ ከበደ በ68 አመቱ ከዚህ አለም በሞት ተለየ፡፡
በገጠመው ህመም ለረዥም ጊዜ አልጋ ላይ ወድቆ የቆየው የቀድሞው አሰልጣኝ ወንድማገኝ ከበደ ባለፈው እሁድ ህዳር 28 ቀን 2ዐ12 ዓ.ም ህይወቱ ያለፈ ሲሆን የቀብር ስነ-ሥርዓቱም ትናንት ሰኞ ኮልፌ ቀራንዮ በሚገኘው ገብርኤል ቤተክርስቲያን ቤተሰቦቹ፣የሙያ ጓደኞቹ፣ወዳጅ ዘመዶቹና የስፖርት ቤተሰቦች በተገኙበት በክብር ተፈፅሟል፡፡
አሰልጣኝ ወንድማገኝ ከበደ ባለፈው እሁድ ይህቺን አለም ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ከመሰናበቱ በፊት ረዘም ላለ ጊዜ በህመም ሲሰቃይ የቆየ ሲሆን ከሀገር ውጭ ህክምና እንዲያገኝ በሀኪሞች ቦርድ ቢወሰንም ለዚያ የሚሆን በቂ ገንዘብ ባለማግኘቱ በሀገር ውሰጥ ሲታከም ቆይቶ በመጨረሻ ህይወቱ ማለፉ ብዙዎችን አሳዝኗል፡፡
ካዛንቺዝ መናኸሪያ አካባቢ ተወልዶ በልዩ ስሙ ቶሎሳ ሠፈር ተብሎ በሚጠራው አካባቢ አብዛኛውን እድገቱን ያሳለፈው አሰልጣኝ ወንድማገኝ ከበደ ሜክሲኮ ለሚባል ቡድን በግብ ጠባቂነት በመጫወት እግር ኳስን አንድ ብሎ የጀመረ ሲሆን ለፈጣን ጎዳና (አውራ ጎዳና)፣ለዳኛው (ሸዋ ፖሊስ)፣ ለኦሜድላ፣ለጥቁር አንበሳ፣ለአንበሳ አውቶብስና በመጨረሻም በወቅቱ በመንግሥቱ ወርቁ በሚሰለጥነው የመብራት ኃይል ቡድንን በግብ ጠባቂነት በማገልገል የጨዋታ ዘመኑን አጠናቋል፡፡
የጨዋታ ዘመኑን በመብራት ኃይል ካጠናቀቀ በኋላ የኤልፓን ወጣት ቡድን በማሰልጠን የስልጠናውን አለም በይፋ የተቀላቀለው አሰልጣኝ ወንድማገኝ ከበደ ከአንደኛ ደረጃ እስከ ካፍ ኤ ላይሰንስ እንዲሁም የኦሎምፒክ ሶሊዳሪቲንና የፊፋ ኃይ ሌቭል አለም አቀፍ ስልጠናዎችን በመውሰድ የአንበሳ ትራንስፖርት፣የመብራት ኃይል፣የእርሻ ሰብል፣ የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ፣የጥቁር አባይ፣የሐረር ቢራ፣የወንጂ፣አዳማና አየር መንገድ የአሰልጣኙን የስልጠና በረከት የቀመሱ ክለቦች ናቸው፡፡
አሰልጣኝ ወንድማገኝ ከበድ ከላይ ከተጠቀሱት ወደ 12 የሚጠጉ ክለቦች በተጨማሪ ሀገሩን በሙያው እንዲያገለግል ጥሪ ተደርጎለት በብሔራዊ ቡድን ደረጀ የወጣት፣የከ17 እና 2ዐ አመት በታች ብ/ቡድኖችን በተለያየ ጊዜ በማሰልጠን ግዴታውን በብቃት ተወጥቷል፡፡
ከአሰልጣኝ ወንድማገኝ ከበደ የስልጠና ህይወት በርካታ የሚጠቀሱ ውጤታማ ጊዜያት ቢኖሩም በተለይ በ1985 ዓ.ም መብራት ኃይልን ለኢትዮጵያ ሻምፒዮና፣የአሸናፊዎች አሸናፊና የፀባይ ዋንጫ ባለቤት ያደረገበት ጊዜ ከሁሉም ስኬቶቹ ከፍ ብሎ የሚነሣ ሲሆን፤ካስመዘገቡት ድል በተጨማሪ በኢትዮጵያ እግር ኳስ ታሪክ ከተገነቡት ምርጥ ቡድንና ምርጥ ተጨዋቾች የተሰባሰቡበት የመብራት ኃይል ቡድን ውስጥ በወቅቱ በድንቅ የጨዋታ እንቅስቃሴያቸው በብዙዎች የሚታወሱት እነ ዳንኤል ክፍሌ፣ተስፊቲን የመሳሰሉ ወጣቶችንም ለእግር ኳሱ አለም ይዘው ብቅ ያሉበት ወርቃማ ጊዜ እንደነበር ይመሰከርላቸዋል፡፡
በተጨዋችነትም በአሰልጣኝነት ዘመኑ ከሁሉም ጋር ተግባቢ፣ትሁትና አመለሸጋ የሆነው አሰልጣኝ ወንደማገኝ ከበደ ከባለቤቱ ከወ/ሮ ሮዛ መሀመድ ጋር በህግ ጋብቻ ፈፅሞ የሶስት ልጆች አባትም ነበር፡፡
አሰልጣኝ ወንደማገኝ ከበደ ለእግር ኳሱ እንደመልፋቱና እንደመድከሙ የውለታውን ያህል ስፖርቱና የሚመለከታቸው አካላት ተገቢውን ምላሽ ሳይሰጡት በቂ ህክምና
ሳይያገኝ በዚህ መልኩ በሞት መነጠቁ ብዙዎችን ያስደነገጠና ያሳዘነ ሲሆን ቀደም ሲል በሌሎች ባለውለተኞች ላይ የታየው ቸልተኝነትና ውለታን መዘንጋት በወንድማገኝ ላይ ተደግሞ መታየቱም ሀዘኑን የበለጠ የከበደ እንዲሆን አድርጎታል፡፡
የሀትሪክ ጋዜጠና ድረ-ገፅ (ዌብ ሳይት) በባለውለተኛው አሰልጣኝ ህልፈተ ህይወት የተሰማንን ጥልቅ ሀዘን እየገለፅን ለቤተሰቦቹ፣ለሙያ ጓደኞቹና ለስፖርት ቤተሰቡ መፅናናትን እየተመኘን አምላክ የሟችን ነፍስ በአፀደ ገነት ያኖርልን ዘንድ እንመኛለን፡፡
አስተያየት ይስጡ