በጎንደር ፋሲለደስ ስታድየም በተደረገው የመጀመሪያ ዙር የመጨረሻ ጨዋታ ፋሲል ከነማ በመሀመድ ናስር ብቸኛ ጎል አርባምንጭን 1ለ0 በማሸነፍ ደረጃውን ማሻሻል ችሏል፡፡
አፄዎቹ ባለፈው ሳምንት በኢትዮጵያ ቡና 3ለ2 ከተሸነፈዉ የቡድን ስብስብ ዉስጥ አንድ ተጫዋች ለውጥ ያደረጉ ሲሆን በቡናዉ ጨዋታ በቀይ ካርድ የወጣው ራምኬሎክ ቦታ ናትናኤል ጋንቹላ በመተካት የተለመደውን 4_2_3_1 አሰላለፍ ተጠቅመው ገብተዋል፡፡
ከወትሮ በተለየ መልኩ የደጋፊ ቁጥር ቀንሶ በታየበት በዚህ ጨዋታ አፄዎቹ የመጀመሪያውን የጨዋታ ክፍለ ጊዜ ሙሉ ብልጫ ወስደው መጫወት የቻሉ ሲሆን ከ5ኛው ደቂቃ ጀምሮ ነበር ወደ ተጋጣሚ የጎል ክልል ውስጥ መድረስ የቻሉት፡፡ ዘንድሮ ቡድኑን የተቀላቀለው መሀመድ ናስር 2 የአርባምንጭ ተከላካዮችን አታሎ በማለፍ ያሻማውን ኳስ ኤፍሬም አለሙ መትቶት ግብ ጠባቂው በቀላሉ ያዳነበት ሲሆን በደቂቃዎች ልዩነት ናትናኤል ጋንቹላ ከርቀት አክሮ የመታው ኳስ በጎሉ አግዳሚ የወጣችው ኳስ በመጀመሪዎቹ 10 ደቂቃዎች አፄዎቹ ያደረጓቸው ለጎል የቀረቡ ሙከራዎች መካከል ሊጠቀሱ ይችላሉ፡፡
ጎል ለማግኘት ይበልጥ ተጭነው የተጫወቱት ፋሲሎች ኤፍሬም አለሙና ኤርሚያስ ሃይሉ በጥሩ ቅብብል ያሻገሯትን ኳስ በጥሩ አቋቋም ላይ የነበረው መሀመድ ናስር አክርሮ በመምታት አፄዎቹን መሪ ማድረግ የምትችል ኳስ ማስቆጠር ችሏል፡፡ ይች ጎል ለመሀመድ ናስር ቡና ላይ ካስመዘገባት ጎል ቀጥሎ ክለቡን ከተቀላቀለ በኃላ ያስቆጠራት ሁለተኛ ጎል ሁና ተመዝግባለታለች፡፡
በአንፃሩ የአፄዎቹ ተጋጣሚ አርባ ምንጭ ከተማዎች በመጀመሪያው አጋማሽ የመጀመሪያ ሙከራ ለማድረግ 35 ያህል ደቂቃዎን የፈጀባቸው ሲሆን 7 ቁጥሩ እንዳለ ከበደ ከርቀት መትቶ በግቡ ቋሚ የወጣችው ኳስ በአዞዎቹ በኩል ብቸኛ የጎል ዕድል ሁና በመመዝገብ የመጀመሪያው አጋማሽ በፋሲል መሪነት ሊጠናቀቅ ችላል፡፡
አዞዎቹ ከእረፍት መልስ መጠነኛ የጨዋታ መሻሻል አድርገው ቢገቡም ኳስን መሐል ሜዳዉ ላይ ከማንሸራሸር ዉጭ ይህ ነዉ ሊባል የሚችል የኳስ ሙከራ ሲያደርጉ አልተስተዋሉም፡፡ በ47ኛዉ ደቂቃ የፊት አጥቂው ፀጋዬ አበራ ከፍፁም ቅጣት ምት መምቻዉ አቅራቢያ መትቷት ወደ ዉጭ ከወጣችዉ ኳስ በስተቀር ሊጠቀስ የሚችል የጎል ሙከራ አላደረጉም፡፡ በተመሳሳይም ፋሲሎች የመሐል አማካዩ ያሳር ሙገርዋ የግል ክህሎቱን በመጠቀም በርካታ የአርባምንጭ ተጫዋቾችን አታሎ በማለፍ ለናትናኤል ጋንቹላ አሻግሮለት ሞክሮ ከመስመር ላይ ከተመለሰችዉ ኳስ በስተቀር ያን ያህል ለጎል የቀረቡ ሙከራዎች ሲያደርጉ አልተስተዋሉም፡፡
በተደጋጋሚ በዳኛ ሲቆራረጥ በነበረውና ሃይል በተቀላቀለበት በዚህ ጨዋታ በፋሲል በኩል1 ቢጫ በአርባምንጭ ደግሞ 3 ቢጫና 1 ቀይ ካርድ የተመዘገቡ ሲሆን ከመጀመሪያው አንፃር የተቀዛቀዘ እና በፋዉሎች የታጀበ ጨዋታ ሁኖ ተጨማሪ ጎል ሳይቆጠርበት በአፄዎቹ 1 ለ 0 አሸናፊነት ተጠናቋል፡፡
የአሰልጣኞች አስተያየት
- ማሰታውቂያ -
ምንተስኖት ጌጡ-ፋሲል ከተማ
“ጨዋታው ጥሩ የሚባል ሲሆን በመጀመሪያው አጋማሽ ሙሉ በሙሉ የኳስ ቁጥጥር ብልጫ በመዉሰድ ጎል ያስቆጠርን ሲሆን የጎል መጠኑን ማስፋት የምንችልበት አጋጣሚ ሳንጠቀምበት ቀርተናል፡፡ በሁለተኛው የጨዋታ ክፍለ ጊዜ ግን ዉጤት ይዞ ለመዉጣት ካለን ፍላጓት የተነሳ ጥንቃቄ የተሞላበት ጨዋታ ያደረግን ሲሆን ከ70 ደቂቃ በኃላ ወደ 4-5-1 ቅርጻችንን በመቀየር መከላከሉ ላይ አመዝነናል፡፡ የመጀመሪያው ዙርን በአሸናፊነት ማጠናቀቃችን ያስደሰተኝ ሲሆን በሁለተኛው ዙር የተጎዱብንና የተቀጡ ተጫዋቾች ተመልሰዉና በመጀመሪያው ዙር የነበሩንን ክፍተት ቀርፈን ጠንካራ ሁነን ለመቅረብ እንሰራለን፡፡”
አሰልጣኝ እዮብ ማለ-አርባምንጭ ከተማ
“ጨዋታዎ በጣም ጥሩ ነበር። ባጠቃላይ ጥሩ ተንቀሳቅሰናል። በቀጣይ ሁለተኛ ዙር ጥሩ ቡድን ይዘን እንቀርባለን።በልጆቼ እንቅስቃሴ ደስተኛ ነኝ”


