ከዛሬው ጨዋታ በኋላ የዋልያዎቹ አለቃ ምን አሉ ?
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ለ2027 የአፍሪካ ዋንጫ ለማለፍ ሳኦቶሜ እና ፕሪንሲፔን በደርሶ መልስ ውጤት 4ለ0 በመርታት ወደ ቀጣዩ ዙር ማለፋቸው ተረጋግጧል። ዛሬ በድሬዳዋ ስታዲየም የመልሱን መርሀግብር ዋልያው አድርጎ 1ለ0 ካሸነፈ በኋላ አሰልጣኝ ዮሐንስ ሳህሌ ለጋዜጠኞች ሀሳባቸውን ሰጥተዋል። አሰልጣኙ በንግግራቸው በአጭር ጊዜ ውስጥ መዘጋጀታቸውን ገልፀው በተለይ ተጫዋቾቹ አዕምሯቸው ላይ ከሜዳ ስራ ባለፈ ሳይኮሎጂ ላይ ትኩረት አድርገው መስራታቸው ውጤቱን ለመያዝ በዋናነት እንደረዳቸው የገለፁ ሲሆን በተለይ በሜዳቸው ደጋፊው በተገኘበት ጨዋታን ማድረግ አቅሙ ቀላል የሚባል እንዳልሆነ ጠቁመው በቀጣይ ግን የምድብ ድልድል ጨዋታ ላይ ትውልደ ኢትዮጵያዊያንን በተመለከተን የሰጡት ሀሳብ ትኩረት ስቧል።

“ትውልደ ኢትዮጵያዊን ተጫዋቾች ባላቸው አቅም ተመውዝነው ወደዚህ መጥተው ሀገራቸውን ቢያገለግሉ ለእኛ እጅግ ትልቅ ጥቅም አለው ፣ ለዚህ ደግሞ ሁሉም ባለ ድርሻ አካላት የበኩላቸው መወጣት አለባቸው” ሲሉ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ዋና አሰልጣኝ ዮሐንስ ሳህሌ ከዛሬው ጨዋታ መጠናቀቅ በኋላ የተናገሩት ሀሳብ ነው።
አስተያየት ይስጡ