በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የመጀመሪያ ዙር ማጠናቀቂያ ጨዋታ ቅዱስ ጊዮርጊስ መሪነቱን ያጠናከረበትን ውጤት አስመዝግቧል።
ኢትዮጵያ ንግድ ባንክን በአዲስ አበባ ስታዲየም የገጠመው የሊጉ መሪ ቅዱስ ጊዮርጊስ 4 ለ 1 በሆነ ውጤት አሸንፏል።ቅዱስ ጊዮርጊስ በመጀመሪያው አጋማሽ አቡበከር ሳኒ፣ አዳነ ግርማ እና ሳላዲን ሰይድ (ሁለት) ባስቆጠሯቸው ግቦች ነው ማሸነፍ የቻለው። ፒተር ንዋድኬ ለንግድ ባንክ ብቸኛዋን ግብ አስቆጥሯል።በዚህም የመጀመሪያውን ዙር እየመራ ማጠናቀቅ የቻለበትን ውጤት አስመዝግቧል። በነገው እለት አዳማ ከተማ ምናልባትም በጣም በሰፊ የግብ ልዩነት ካሸነፈ መሪነቱን ከቅዱስ ጊዮርጊስ ሊነጥቅ ይችላል። በሌላ በኩል አዲስ አበባ ከተማ እና ወልዲያ ከተማ ያደረጉት ጨዋታ 1 ለ 1 በሆነ አቻ ውጤት ተጠናቋል።
ወልዲያ ጫላ ድሪባ በ45ኛው ደቂቃ ባስቆጠራት ግብ ቀዳሚ ቢሆንም፥ ከእርፍት መልስ ዳዊት ማሞ ያስቆጠራት ጎል በፕሪሚየር ሊጉ የደረጃ ሰንጠረዥ ግርጌ ላይ የሚገኘውን አዲስ አበባ ከተማን አቻ ማድረግ ችላለች። እሁድ ስድስት ጨዋታዎች በተለያዩ ከተሞች ይስተናገዳሉ።
በአዲስ አበባ ስታዲየም መከላከያ ሲዳማ ቡናን 9 ሰዓት ላይ ሲያስተናግድ፥ ክልል ላይ ጅማ አባቡና ከድሬዳዋ፣ አርባምንጭ ከተማ ከኢትዮጵያ ቡና፤ ፋሲል ከተማ ከአዳማ ከተማ በተመሳሳይ 9 ሰዓት ላይ ይጫወታሉ። 10 ሰዓት ላይ ደግሞ በአዲስ አበባ አበበ ቢቂላ ስታዲየም ደደቢት ከወላይታ ዲቻ ይገናኛሉ። 11 ሰዓት 30 ላይ ደግሞ ኢትዮ ኤሌክትሪክ ከሀዋሳ ከተማ በአዲስ አበባ ስታዲየም የሚጫወቱ ይሆናል።
















አስተያየት ይስጡ