በኢትዮጵያ ከፍተኛ ሊግ በመሳተፍ ላይ የሚገኘው ስሑል ሽሬ የእግር ኳስ ቡድን ከ1 ነጥብ 8 ሚሊዮን ብር በላይ ዋጋ ያለው ዘመናዊ አውቶቡስ በእርዳታ አገኘ።
ዘመናዊ አውቶቡሱን ለቡድኑ ያበረከተው በሽሬ እንዳስላሴ ከተማ የሚገኝ የዳሽን ቢራ ማከፋፈያ አክሲዮን ማህበር ነው።
በስጦታ የተገኘው ዘመናዊ አውቶብስ የእግር ኳስ ቡድኑ ቀደም ሲል የነበረበትን የትራንስፖርት ችግር እንደሚፈታለት የክለቡ ምክትል አስልጣኝ በረከት ገብረመድህን ገልፀዋል።
ከዚህ በተጨማሪ አውቶብሱ የተጫዋቾችን ሞራል ለመገንባትና ከቦታ ወደ ቦታ በምቾት ለመጓጓዝ ጠቀሜታ እንዳለው ነው የገለጹት።
ለተለያዩ ድርጅቶች በተደጋጋሚ ያቀረቡትን የተሽከርካሪ ድጋፍ ጥያቄ ማህበሩ በአግባቡ ሰምቶ ዘመናዊ አውቶቡስ በማበርከቱ ከፍተኛ ደስታ እንደተሰማው የገለጸው ደግሞ የቡድኑ አምበል ወጣት መብራህቶም ፍስሃ ነው።
ዘመናዊ አውቶቡሱ ባለ 49 መቀመጫ ወንበር፣ ፍሪጅ፣ የሻይ ማሞቂያ ማሽንና ቴሌቪዥን የተገጠመለት ነው።
የማህበሩ ሥራ አስኪያጅ አቶ መኮነን ገብረሕይወት በበኩላቸው የእግር ኳስ ቡድኑ ያለበትን የትራንስፖርት ችግር ለመቅረፍ ሲባል ዘመናዊ አውቶቡሱን ገዝተው ድጋፍ ማድረጋቸውን ገልጸዋል።
በተጨማሪም አውቶቡሱ የእግር ኳስ ቡድኑ ከከፍተኛ ሊግ ወደ ፕሪሚየርሊግ እንዲያድግ በሚደረገው ጥረት የበኩላቸውን ድጋፍ ለማበርከት በሚል እሳቤ መሆኑንም ተናግረዋል።
እንደአቶ መኮንን ገለጻ ቀደም ሲልም ማህበሩ ከ200 ሺህ ብር በላይ በጥሬ ገንዘብ ለእግር ኳስ ብድኑ ድጋፍ አድርጓል።
ስሑል ሽሬ የእግር ኳስ ብድን ሁለት ተስተካካይ ጨዋታዎች እየቀረው ከምድቡ በስድስተኛ ደረጃ ላይ ይገኛል።
Source-ENA

አስተያየት ይስጡ