በአፍሪካ ቻምፒየንስ ሊግ የቅድመ ማጣሪያ የሚልስ ጨዋታ የግብፁን አልአህሊን በአ/አ ስታዲየም ያስተናገደው ጅማ አባጅፋር 1-0 በሆነ ውጤት ቢያሸንፍም በደርሶ መልስ ውጤት 2-1 ተሸንፎ ሳያልፍ ቀርቷል።
በጨዋታው የመጀመሪያውን ሙከራ በማድረግ ረገድ እንግዳዎቹ ቀዳሚ የነበሩ ሲሆን 5ኛው ደቂቃ ላይ የአልአህሊው ሙሀርብ አክርሮ የመታው ኳስ በግቡ አናት ላይ ወደ ውጭ ወጥቷል። 14ኛው ደቂቃ ላይ የጅማ አባጅፋሩ ዲዲዬ ለብሪ ያሻማውን ኳስ አፒያ ወደ ግብ ሞክሮት ግብ ጠባቂው አውጥቶበታል። በተደጋጋሚ ወደ አልአህሊ የግብ ክልል ለመድረስ ጥረት ሲያደርጉ የነበሩት ጅማ አባጅፋሮች ተደጋጋሚ ሙከራ ማድረግ ችለው ነበር። ይህን ተከትሎም 34ኛው ደቂቃ ላይ ኄኖክ ገምቴሳ ተከላካዮችን አታሎ ከሳጥን ውጪ ያደረገው ሙከራ ኢላማውን ሳይጠብቅ ወደ ውጪ ወጥቷል።

አልአህሊዎች ከሜዳቸው ውጪ እንደመጫወታቸው እና ውጤቱን ለማስጠበቅ ጥንቃቄ የተሞላበት ጨዋታ ሲጫወቱ ተስተውለዋል። 35ኛው ደቂቃ ላይ የአልአህሊው ኢስላም ሙሀርብ የሞከረው ኳስ በግቡ አናት ላይ ወጥቶበታል። ሆኖም ግን የመጀመሪያው አጋማሽ ሊጠናቀቅ በተቃረበበት ሰዓት እና የዳኛው ፊሽካ እየተጠበቀ በነበረበት ሰዓት የጅማ አባጅፋሩ አስቻለው ግርማ ያሻገረለትን ኳስ ዲዲዬ ለብሪ ወደግብነት ቀይሮት የመጀመሪያው አጋማሽ በጅማ አባጅፋር 1-0 መሪነት ተጠናቆ ሁለቱ ቡድኖች ወደ መልበሻ ቤት አምርተዋል።

ሁለተኛው አጋማሽም እንደመጀመሪያው አጋማሽ ሁሉ ጥሩ ጥሩ ሙከራዎች የተደረጉበት ነበር። በዚህኛውም አጋማሽ ጅማ አባጅፋር ተጭነው ሁለተኛ ግብ ለማግኘት ሲረባረቡ ተስተውለዋል። 53ኛው ደቂቃ ላይ ተቀይሮ የገባው ኦሊድ አዛሮ የጅማን ተከላካዮች መዘናጋት ተከትሎ ያገኘውን ኳስ ወደ ሳጥን ውስጥ ይዞ በመግባት አክርሮ ሲመታ ይሁን እንዳሻው ተደርቦ አውጥቶበታል። 60ኛው ደቂቃ ላይ የጅማ አባጅፋሩ ማማዱ ሲዲቤ ከይሁን እንዳሻውየተቀበለውን ኳስ በቀጥታ ሲሞክር የአል አህሊ ተከላካዮች ተደርበው አውጥተውበታል። 66ኛው ደቂቃ ላይ የአልአህሊው ሂሻም መሀመድ በረጅሙ ያሻማውን ኳስ ኦሊድ አዛሮ የአጃዬን ቦታውን ለቅቆ መውጣት ተመልክቶ በግንባሩ የሞከረውን ኳስ ግብ ጠባቂው ዳንኤል አጃዬ እንደምንም አድኖበታል።
አልፎ አልፎ ወደጅማ የግብ ክልል ሲደርሱ የነበሩት አል አህሊዎች 73ኛው ደቂቃ ላይ የመሀል ተከላካዩ ሳሊፍ ኩሊባሊ ያገኘውን ኳስ ወደ ግብ ሞክሮት የጅማ አባጅፋሩ ግብ ጠባቂ ዳንኤል አጄዬ አድኖበታል። ጨዋታው ሊጠናቀቅ 6ደቂቃዎች ሲቀሩት 84ኛው ደቂቃ ላይ ተቀይሮ የገባው የጅማ አባጅፋሩ ማማዱ ሲዲቤ ከሳጥን ውጪ አክርሮ የሞከረው ኳስ ለጥቂት ወደ ላይ ወጥቷል። 88ኛው ደቂቃ ላይ የአል አህሊ ኦሊድ አዛሮ ከኢስላም ሙሀርብ የተሻገረለትን ኳስ ወደ ግብ ሞክሮት ለጥቂት በግቡ ቋሚ በኩል ወጥቶበታል።

ጨዋታውም በዚሁ ውጤት ተጠናቆ ጅማ አባጅፋር በድምር ውጤት 2-1 ተሸንፎ ወደ ምድብ ድልድሉ መግባት ሳይችል ቀርቷል። ጅማ አባጅፋር ከቻምፒየንስ ሊጉ ቢባረርም በኮንፌደሬሽን ካፕ የመካፈል እድል ይኖረዋል። በዚህም አንድ የደርሶ መልስ ጨዋታ በማድረግ አሸናፊ የሚሆን ከሆነ ወደ ኮንፌዴሬሽን ካፕ ምድብ ድልድል ለመግባት ይችላል።
አስተያየት ይስጡ