– በሊጉ የ16ተኛ ሳምንት የሶስተኛ ዕለት ቀዳሚ ጨዋታ ቅዱስ ጊዮርጊስ ወልቂጤ ከተማን አሸንፏል ።
128ተኛዉን የአድዋ ድል በዓል በመዘከር በጀመረዉ የዕለቱ የመጀመሪያ ጨዋታ በተለይ በመጀመሪያው አጋማሽ ምንም እንኳን በሙከራ ረገድ ደካማ የነበረ ቢሆንም በእንቅስቃሴዉ መባቻ ላይ ግን አዲሱ ፈራሚ ታምራት በ14ተኛዉ ደቂቃ ላይ ከቢኒያም በላይ የተቀበለዉን ኳስ በቀጥታ ወደ ግብ ሞክሮ የነበረ ቢሆንም ፈጥኖ የወጣዉ የግብ ዘቡ ፋሪስ አለሙ ኳሷን አውጥቷታል። በድጋሚ ከአራት ደቂቃዎች በኋላ ደግሞ ከቀኝ መስመር በኩል ሄኖክ አዱኛ የሞከረዉን ኳስ ተጨርፎ ሲመለስ ያገኘዉ ዳግማዊ አርአያ በቀጥታ ወደ ግብ ሞክሮ የግብ ዘቡ ፋሪስ አውጥቷል።
ተደጋጋሚ ሙከራዎችን በማድረግ ግብ ለማስቆጠር ሲጥሩ የነበሩት ጊዮርጊሶች በአጋማሹ መገባደጃ ተከላካዩ ረመዳን የሱፍ ከቢኒያም የተቀበለዉን ኳስ በቀጥታ ወደ ግብ ሞክሮ ኳሷ ኢላማዋን ሳትጠብቅ ወጥታለች ። ምንም እንኳን በጨዋታ እንቅስቃሴ የተሻለ ቢሆንም በሙከራ ረገድ ግን ሶስት ኢላማቸዉን የጠበቁ ሙከራዎች ብቻ በተደረጉበት እና ግብ ባልተስተናገደበት የመጀመሪያው አጋማሽ ክትፎዎቹ ይህ ነዉ የሚባል ተጠቃሽ ሙከራ ሳያደርጉ ለዕረፍት ወደ መልበሻ ክፍል አምርተዋል ።
- ማሰታውቂያ -
ከዕረፍት መልስ የሁለት ተጫዋቾችን ለዉጥ አድርገዉ የገቡት ፈረሰኞቹ ዉጥናቸዉ ሰምሮ በ62ተኛዉ ደቂቃ ላይ ተቀይሮ በገባዉ አማኑኤል አረቦ አማካኝነት ግብ ማስቆጠር ችለዋል ፤ በዚህም ከቀኝ መስመር በኩል ቢኒያም ያሻማዉን ኳስ አማኑኤል አረቦ በግንባሩ ግጭቶ ወደ ግብነት በመቀየር ክለቡን መሪ አድርጓል።
በሙከራ ረገድ ያን ያህል ባልነበሩት ክትፎዎቹ በኩል በ64ተኛዉ ደቂቃ ላይ ጋዲሳ መብራቴ ያሻማዉን ኳስ ሙሉዓለም መስፍን ወደ ግብ ቢሞክርም ባህሩ ነጋሽ ይዞበታል ። በጥሩ ፉክክር በቀጠለዉ መርሐግብር በመገባደጃዉ ወቅት በበረከት ወልዴ አማካኝነት ድንቅ ሙከራ ማድረግ የቻሉት ጊዮርጊሶች በጭማሪ ደቂቃ ላይ ሁለተኛዋን የማሸነፊያ ጎላቸዉን ተቀይሮ በገባዉ አልዓዛር አማካኞነት አስቆጥረዉ ጨዋታውን 2ለ0 ማሸነፍ ችለዋል ።
– በምሽቱ የአንድ ሰዓት መርሐግብር በወራጅ ቀጠናዉ ላይ የሚገኘዉ ሻሸመኔ ከተማ ከመመራት ተነስቶ ወላይታ ዲቻን 2ለ1 በሆነ ዉጤት ማሸነፍ ችሏል ።
ድንቅ ፉክክር ባስመለከተን እና እንደ መጀመሪያዉ ጨዋታ ሁሉ በአደዋ ድል መዘከር በጀመረዉ የምሽቱ ጨዋታ ዲቻዎች ገና በመባቻዉ በዘላለም አባተ አማካኝነት ግብ ለማስቆጠር ተቃርበዉ ግቀሰ ጠባቂዉ አቤል ማሞ አውጥቶባቸዋል። ጫናቸዉን አጠንክረዉ የቀጠሉት ዲቻዎች በድጋሚ ከደቂቃዎች በኋላ ብስራት በቀለ ከዘላለም በተቀበለው ኳስ ድንቅ ሙከራ ቢያደርግም ኳሷ በግቡ አናት ለጥቂት ወጥታለች።
ተደጋጋሚ ሙከራ ማድረግ የቀጠሉት ድሬዎች በ16ተኛዉ ደቂቃ ላይ ቢኒያም ፍቅሬ ከርቀት ድንቅ ሙከራ አድርጎ ግብ ዘቡ አቤል ሲያወጣበት በድጋሚ በ33ተኛዉ ደቂቃ ላይ አብነት ደምሴ በግንባር ሞክሮ ኳሷ ለጥቂት ወጥታለች ። በመጀመሪያዉ አጋማሽ መገባደጃ ወቅት በ45ተኛዉ ደቂቃ ላይም ኬኔዲ ከበደ ከቀኝ መስመር በኩል ያሻገረዉን ኳስ ቢኒያም ፍቅሬ ወደ ግብነት ቀይሮ ዲቻዎችን መሪ ማድረግ ችሏል።
ከዕረፍት መልስ ተሻሽለዉ የተመለሱት ሻሸመኔ ከተማዎች በቶሎ የአቻነት ግብ ማስቆጠር ችለዋል ፤ በዚህም በ52ተኛዉ ደቂቃ ላይ ከአብዱልቃድር ናስር የተቀበለዉን ኳስ አዲሱ ፈራሚ ስንታየሁ ወደ ግብነት ቀይሮ ክለቡን አቻ ማድረግ ችሏል። ከመጀመሪያው አጋማሽ ይልቅ መቀዛቀዝ የታየባቸዉ ዲቻዎች በአጋማሹ በ63ተኛዉ ደቂቃ ላይ በቢኒያም ፍቅሬ አማካኝነት ከርቀት ተጠቃሽ ሙከራ ማድረግ ችለዋል ።
በሙከራም በጨዋታ እንቅስቃሴም ረገድ የተሻሉ የነበሩት ሻሸመኔዎች በ73ተኛዉ ደቂቃ ላይ መሪ መሆን የቻሉበትን ግብ አስቆጥረዋል ፤ በዚህም ሀብታሙ ንጉሴ ከቅጣት ምት ያሻማዉን ኳስ አሸናፊ ጥሩነህ በቀላሉ ወደ ግብነት ቀይሮ ክለቡን ሻሸመኔ አሸናፊ ማድረግ ችሏል።