ቀን ዘጠኝ ሰዓት ሲል በጀመረዉ የወላይታ ዲቻ እና ሀድያ ሆሳዕና ጨዋታ የጦና ንቦቹ ከመመራት ተነስተዉ ተጋጣሚያቸዉን ማሸነፍ ችለዋል።
በፈጣን የሜዳ ላይ እንቅስቃሴ እና ቶሎ ቶሎ በሚደረጉ ሽግግሮች በጀመረዉ የሁለቱ ክለቦች የዕለቱ የመጀመሪያ ጨዋታ ገና በመባቻዉ ግብ ተቆጥሮበታል ። በዚህም በ10ኛዉ ደቂቃ ላይ ከቅጣት ምት የተገኘዉን ኳስ ሳሙኤል ዮሐንስ በግራ መስመር በኩል ይዞ ገብቶ ወደ ሳጥን ሲያሻግር ኳሷን ያገኛት ተመስገን ብርሀኑ ወደ ግብነት ቀይሮ ክለቡን መሪ ማድረግ ችሏል።
በጊዜ ከተቆጠረችዉ ግብ በኋላ እምብዛም ሙከራዎችን ባላስመለከተን የጨዋታዉ እንቅስቃሴ ናታን ጋሻዉ በወላይታ ዲቻ በኩል እና ዳዋ ሆቴሳ ደግሞ በሀድያ ሆሳዕና በኩል እጅጉን ለግብ የቀረበ ተጠቃሽ ሙከራ ማድረግ ቢችሉም ጨዋታዉ ተጨማሪ ግብ ሳያስመለክተን ኢጋማሹ ተጠናቋል።
ከዕረፍት መልስ በተሻለ እንቅስቃሴ በጀመረዉ የሁለቱ ክለቦች ጨዋታ በ56ተኛዉ ደቂቃ ላይ የወላይታ ዲቻዉ የመስመር ተጫዋች ብስራት በቀለ ያቀበለዉን ኳስ አማካዩ አብነት ደምሴ በግሩም ሁኔታ ወደ ግብነት ቀይሮ ክለቡን አቻ ማድረግ ችሏል።
- ማሰታውቂያ -
የአቻነት ግብ ካስቆጠሩ በኋላ በጥሩ መነሳሳት መጫወታቸውን የቀጠሉት ወላይታ ዲቻዎች በተለይ ወደ መጨረሻዎቹ ደቂቃዎች ላይ ጫና ፈጥረዉ በመጫወት ተደጋጋሚ ሙከራዎችን ማድረግ የቀጠሉ ሲሆን ጥረታቸዉ ፍሬ አፍርቶም በ82ተኛዉ ደቂቃ ላይ ግብ አስቆጥረዉ ከመመራት ተነስተዉ ሀድያ ሆሳዕናን 2ለ1 በሆነ ዉጤት ማሸነፍ ችለዋል።
በዕለቱ ሁለተኛ ጨዋታ ኢትዮጵያ መድን ሻሸመኔ ከተማን ሁለት ለዜሮ በሆነ ዉጤት ማሸነፍ ችሏል።
ያን ያህል ማራኪ የጨዋታ እንቅስቃሴን ባላስመለከተን የምሽቱ የሁለቱ ክለቦች ጨዋታ በመጀመሪያዎቹ ደቂቃዎች ላይ ሁለቱም ክለቦች ተጠቃሽ ሙከራ ለማድረግ ሲቸገሩ የተስተዋለ ሲሆን አልፎ አልፎ ግን ኢትዮጵያ መድን ጫናዎችን ለመፍጠር እና ሲጥሩ ተስተውሏል። በዚህ አይነት እንቅስቃሴ በጀመረው ጨዋታ ግብ ሳይቆጠርበት አጋማሹ ሊጠናቀቅ ሲል ግን መድኖች መሪ መሆን የቻሉበትን ግብ ማስቆጠር ችለዋል።
በዚህም በ45ተኛዉ ደቂቃ ላይ ከወደ ቀኝ መስመር በኩል የቀኝ ተመላላሹ አብዱልከሪም መሐመድ ወደ ሳጥን የላከዉን ኳስ የሻሸመኔ ከተማዉ ተከላካይ ምንተስኖት ከበደ በሚገባ ማፅዳት ባለመቻሉ ምክንያት ኳሷ በራሱ ግብ ላይ አርፋ መድኖች አጋማሹን በመሪነት አገባደዋል።
በሁለተኛዉ አጋማሽ የተሻለ እንቅስቃሴ ሁለቱም ክለቦች ያስመለከቱን ሲሆን በሙከራ ረገድም የተሻለ ነገር ተመልክተንበታል ። በዚህም በአጋማሹ መገባደጃ ወቅት ግብ የተቆጠረባቸዉ ሻሸመኔ ከተማዎች የአቻነት ግብ ለማስቆጠር በተደጋጋሚ በእነ ሁዛፍ አሊ እና የቡድን አጋሮቹ አማካኝነት ጥረት ቢያደርጉም ነገር ግን ጥረታቸዉ ሳይሳካ ቀርቶ ይባስኑ በ90+2 ላይ አጥቂዉ ስንታየሁ መንግስቱ ሞክሮ ግብ ጠባቂዉ የመለሳትን ኳስ ሌላኛዉ ተቀይሮ የገባዉ አጥቂ አብዲሳ ጀማል ወደ ግብነት ቀይሮ ክለቡ ሁለት ለዜሮ እንዲያሸንፍ አስችሏል።