የመጀመሪያዉ አጋማሽ በሁለቱም በኩል ጨዋታዉ በቀዝቃዛ እንቅስቃሴ የጀመረ ሲሆን ወላይታ ዲቻዎች እየተከላከሉ ከሜዳቸዉ በመልሶ ማጥቃት ወደፊት እየተጫወቱ ወደ ቅዱስ ጊዮርጊሶች የግብ ክልል ለማምራት ጥረት ሲያደርጉ የነበረ ሲሆን ጊዮርጊሶች በበኩላቸዉ ኳስን መስርቶ በመጫወት በተለያዩ አቅጣጫዎች ወደ ወላይታ ዲቻ የሜዳ ክፍል አዘምነዉ ለመጫወት ጥረት ሲያደርጉ ነበር።
የወላይታ ዲቻዉ የቀኝ መስመር ተከላካይ ያሬድ ዳዊት አቤል ያለዉ ላይ በፈፀመው ጥፋት በ36ኛዉ ደቂቃ በሁለት ቢጫ ከሜዳ የተሰናበተ ሲሆን ቅዱስ ጊዮርጊሶች ይሄንን አጋጣሚ በመጠቀም ወላይታ ዲቻዎች ላይ ተጭነው በመጫወት ጎል ለማስቆጠር ጥረት ሲያደርጉ የነበረ ቢሆንም ነገር ግን ሳይሳካላቸዉ ቀርቶ ጨዋታው በ0-0 የአቻ ዉጤት ወደ መልበሻ ክፍል አምርቷል።
ከእረፍት መልስ ወደ ሜዳ ሲመለሱ ወላይታ ዲቻዎች ቃልኪዳን ዘላለምን በአናጋዉ ባደግ በመቀየር ወደ ጨዋታዉ ሜዳ የገቡ ሲሆን ጨዋታዉ ከመጀመሪያዉ አጋማሽ በተሻለ መልኩ በጥሩ መነቃቃት ነበር የጀመረዉ።
- ማሰታውቂያ -
ሁለቱም ክለቦች ከመጀመሪያዉ አጋማሽ በተሻለ መልኩ የማጥቃት አጨዋወት ሲያዘወትሩ የነበረ ሲሆን በተደጋጋሚ አንዳቸዉ ወደ አንዳቸዉ የግብ ክልል በማምራት ለጎል የሚሆኑ ኳሶችን ሲሞክሩ ነበር። ነገር ግን በአንፃራዊነት ኳስን ተቆጣጥሮ በመጫወቱ ረገድ ቅዱስ ጊዮርጊሶች የተሻሉ የነበረ ሲሆን በ62ኛው ደቂቃ ከሔኖክ በረጅሙ ወደ ጎል የተሻማለትን ኳስ ቸርነት ጉግሳ በግንባሩ በመግጨት ወደ ግብነት ቀይሯት ጨዋታዉ በቅዱስ ጊዮርጊት የ1-0 መሪነት መቀጠል ችሏል።
ቅዱስ ጊዮርጊሶች አሁንም ተጭነዉ መጫወታቸዉን ቀጥለዉ 78ኛው ደቂቃ ላይ በእስማኤል ኦሮ አጎሮ በኩል ባስቆጠሯት ጎል ጨዋታዉን 2-0 በሆነ ዉጤት መምራታቸዉን ቀጠሉ።
ወላይታ ዲቻዎች የመጨረሻዎቹን ደቂቃዎች ተጭነዉ በመጫወት ወደ ቅዱስ ጊዮርጊስ የግብ ክልል ደጋግመዉ ማምራት የቻሉ ሲሆን ከሽንፈት ያልታደገቻቸዉን 1 ጎል በ82ኛው ደቂቃ ላይ በረከት ወልደዩሀንስ በግንባር ገጭቶ አስቆጥሮላቸዉ ጨዋታዉ በቅዱስ ጊዮርጊስ 2-1 በሆነ ዉጤት ተጠናቋል።
በዚህም መሰረት ቅዱስ ጊዮርጊሶች ከተከታያቸዉ ባህርዳር ከነማ ጋር ያላቸዉን የነጥብ ልዩነት ወደ 5 ከፍ ማድረግ ችለዋል።