17ተኛዉ የአዲስአበባ ከተማ ዋንጫ ዛሬም ቀጥሎ ሲከናወን በአራተኛ ቀን ውሎዉ የአምናዉ ሻምፒዮን ቅዱስ ጊዮርጊስ በኢትዮጵያ መድን ሽንፈት አስተናግዷል።
በዕለቱ ብቸኛ በነበረዉ እና ቀን 7:00 ሰዓት ላይ በተደረገዉ ተጠባቂ መርሐግብርም አምና ባደገበት አመት አስደናቂ ጊዜን ማሳለፍ የቻለዉ የአሰልጣኝ ገብረመድህን ሀይሌ ቡድን ኢትዮጵያ መድን በቀኑ ጨዋታ ገና በዘጠነኛዉ ደቂቃ ላይ በአምበሉ ሀቢብ ከማል አማካኝነት መሪ መሆን ችሏል። ከግቧ መቆጠር በኋላም ወደ ጨዋታዉ ለመመለስ በቶሎ ጥረት ማድረግ የቻለዉ ቅዱስ ጊዮርጊስ በአጥቂዉ ሀብታሙ ጉልላት አማካኝነት በ14ተኛዉ ደቂቃ ላይ የአቻነት ግብ ማስቆጠር ችሏል።
- ማሰታውቂያ -
በዚህ ሂደት የቀጠለዉ የሁለቱ ክለቦች ጨዋታም የመጀመሪያዉ አጋማሽ ሊጠናቀቅ ሶስት ያህል ደቂቃዎች በቀሩበት ወቅትም ሀቢብ ከማል ሁለተኛ ጎል በማስቆጠር ክለቡን መሪ ማድረግ ችሏል። ከዕረፍት መልስ ሁለቱም ክለቦች በተመሳሳይ ተጨማሪ ግብ ለማስቆጠር እንቅስቃሴ ሲያደርጉ የነበረ ሲሆን መደበኛዉ ዘጠና ደቂቃ ተጠናቆ በጭማሪ ደቂቃ ላይም ወገኔ ገዛኸኝ ለመድን ሶስተኛ ግብ አስቆጥሮ ጨዋታዉ በኢትዮጵያ መድን 3ለ1 አሸናፊነት ተጠናቋል።