በኢትዮጵያ ፕሪሜየር ሊግ 6ኛ ሳምንት ጨዋታ ሁለቱን የበርካታ ደጋፊዎች ባለቤት የሆኑትን ኢትዮጵያ ቡና እና ቅዱስ ጊዮርጊስን አገናኝቶ በአቻ ውጤት ሊጠናቀቅ ችሏል፡፡
ከጨዋታው አስቀድሞ የሁለቱም ቡድን ተጫዋቾች ከተለምዶ ወጣ ባለ መልኩ ኢትዮጵያ ቡና በግራ ጥላ ፎቅ ቅ/ጊዮርጊሶች ደግሞ በቀኝ ጥላ ፎቅ ከመልበሻ ክፍል በመውጣት ለደጋፊዎቻቸው ስፖርታዊ ጨዋነትን ” እግር ኳስ ላብ እንጂ ደም አይፈልግም” የሚል መሪ ቃል ይዘው ተቃራኒ ደጋፊዎችን ሰላምታ በመስጠት ወደ ልምምድ ወጥተዋል፡፡

11:07 ሲል የኢትዮጵያ ብሔራዊ መዝሙር በመዘመር የተጀመረው የሁለቱ ቡድኖች ጨዋታ በኢትዮጵያ ቡና በኩል በ4-4-2 አሰላለፍ እንዲሁም በቅዱስ ጊዮርጊስ በኩል በ4-3-3 አሰላለፍ ሲቀርቡ ከመጀመርያው የዳኛ ፊሽካ መነፋት ጀምሮ ኢትዮጵያ ቡና ከተጋጣሚው ከቅዱስ ጊዮርጊስ የተሻሉ ነበሩ፡፡
የመጀመሪያውን 20 ደቂቃዎች መሀል ሜዳና ክንፍ ላይ ያገደለን ጨዋታ ሲያሳዩ በ21ኛው ደቂቃ ላይ ሳሙኤል ሳኑሚ ከመሀል ሜዳ የተሻገረለት ኳስ ሳልሀዲን ባርጌቾን በጥሩ ሁኔታ በማለፍ የሞከራትን ኳስ የቅዱስ ጊዮርጊሱ ግብ ጠባቂ ሮበርት ኦዶንኮራ ያዳነበት ኳስ በመጀመሪያው አጋማሽ ለጎል የቀረበ ሙከራ ነበር፡፡ ከዚህ ሙከራ በኋላ በአብዛኛው በቀኝ መስመር በኩል ያጋደለን ኳስ መርጠው ሲጫወቱ ተስተውሏል፡፡

30ኛው ደቂቃ ላይ ኢብራሂም ፎፎና በሰራው ጥፋት ቢጫ ካርድ ሊመለከት ችሏል፡፡ የመጀመሪያው አጋማሽ በዚሁ 0-0 ውጤት ወደ መልበሻ ክፍል ሊያመራ ችሏል።
በሁለተኛው አጋማሽ በኢትዮጵያ ቡና አማካኝነት ኳስ ሲጀመር የመጀመሪያውን ሙከራ ከ4 ደቂቃዎች በኃላ ከቀኝ መስመር የተሻማውን ኳስ በኃይሉ አሰፋ በመቀስ ምት የሞከራት ኳስ በግቡ አግዳሚ አናት ላይ ሊወጣ ችሏል፡፡ ከጎልዋ ሙከራ በኃላ ቅ/ጊዮርጊስ በተሻለ ለመንቀሳቀስ የሞከሩ ሲሆን የቡናን የተከላካይ ክፍል ማለፍ ተስኗቸው ተስተውሏል፡፡ በ60ኛ ደቂቃ ላይ አሜ መሀመድ ባጋጠመው ጉዳት ለመቀየር ተገዷል፡፡ ከ70ኛ ደቂቃ በኃላ ጥንቃቄ የታከለበት እና ይሄነው የሚባል ሙከራ ያልታየበት የሁለቱ ቡድኖች ጨዋታ በአቻ ውጤት ተጠናቋል፡፡
የአሰልጣኞች አስተያየት
የቅ/ጊዮርጊሱ ም/አሰልጣኝ ፋሲል ተካልኝ

”በመጀመሪያው አጋማሽ ጥሩ አልነበርንም። በሁለተኛው አጋማሽ ከመጀመሪያው አጋማሽ የተሻለ ለመንቀሳቀስ ሞክረናል። ነገር ግን በሙሉ ጨዋታው የሚገባንን ያህል ተጫውተናል ብዬ አላስብም። ” ሲል አስተያየቱን ሲሰጥ
የኢ.ቡናው አሰልጣኝ ሀብተወልድ ደስታ በበኩሉ
en
“ጨዋታውን ሙሉ ለሙሉ ለመቆጣጠር ጥረት አድርገናል። የተሻለ ጨዋታም ተጫውተናል። ውጤቱም ይገባን ነበር። ሆኖም የጨዋታው አጋጣሚ ያሳየንን ነገር ተቀብለናል።” በማለት አስተያቱን አጠቃሏል።


አስተያየት ይስጡ