በኢትዮጵያ ኘሪሜየር ሊግ 19ኛ ሳምንት የመጨረሻ ጨዋታ በኮንፌደሬሽን ካኘ ኢትዮጵያን ወክሎ እየተሳተፉ እሚገኘው ወላይታ ድቻና ሃዋሳ ከተማ አንድ ለአንድ በሆነ አቻ ውጤት ተለያዩ፡፡
ጨዋታው እንደተጀመረ በ3ኛ ደቂቃ ላይ ጎል ማስቆጠር የቻሉት ወላይታ ድቻዎች ሲሆኑ ጃኮ አራፋት ግቧን በስሙ ማስመዝገብ ችሏል።
በመጀመሪያው የጨዋታ አጋማሽ ኳስን መስርቶና ተቆጣጥሮ ወደ ግብ በመድረስ እንግዳው ሀዋሳ ከተማ የተሻሉ ነበሩ።
በአንፃሩም ድቻዎች ከኳስ ኃላ በመሆን አፈግፍገው መጫወትን ምርጫቸው በማድርግ የመጀመሪያው አጋማሽ በ1-0 መሪነት ወደ መልበሻ ክፍል አምርተዋል።

በሁለተኛው የጨዋታ ክፍለ ግዜ ባለሜዳዎቹ የጦና ንቦቹ ኳስን ተቆጣጥሮ ወደ ተጋጣሚ ግብ ክልል በመድረስ የተሻሉ ነበሩ።
ሃዋሳ ከተማ በአንፃሩ የመሀል ሜዳውን ክፍል በመቆጣጠር መልካም የሚባል የኳስ እንቅስቃሴ አሳይቷል፡፡
በ61ኛው ደቂቃ ላይ የወላይታ ድቻ የኃላ ደጀን ሙባሪክ ሽኩር በራሱ ላይ ያስቆጠረው ግብ ሃዋሳ ከተማ አቻ እንዲሆን አስችሎታል።
ግቧ ከተቆጠረች ከ25ደቂቃዎች በኃላ በደጋፊዎቻቸው መካከል በተፈጠረ ረብሻ ጨዋታው ለተወሰኑ ደቂቃዎች ሊቋረጥ ተገዷል። በተነሳውም ረብሻ የተወሰኑ የሁለቱም ክለብ ደጋፊዎች ጉዳት ሊደርስባቸው ችሏል።በመጨረሻም በፀጥታ ሀይሎች ደጋፍ ጨዋታዎ ቀጥሎ 1-1 በሆነ አቻ ውጤት ጨዋታው ተጠናቋል።
የአሰልጣኞች አስተያየት
አሰልጣኝ ዘነበ ፍስሀ -ወላይታ ድቻ
” ወደ ተጋጣሚያችን የግብ ክልል ደጋግመን መድረስ ብንችልም ወደ ጎል የመቀየር ችግር ነበረብን።
በቀጣይም ይህንን ስህተታችን በማስተካከል ወደ አሸናፊነት ለመመለስ እንሰራለን ።”
አሰልጣኝ ውበቱ አባተ -ሀዋሳ ከተማ
“ከወላይታ ድቻ ጋር የሚደረገው ጨዋታ ከባድ እንደሚሆን ጠብቀነው ነበር፤ ከምንም በላይ ከሜዳ ውጪ ነጥብ በመጋራታችን ደስ ብሎኛል።”
አስተያየት ይስጡ