ኢትዬጵያ ቡና ከሜዳው ውጭ በሳሙኤል ሳኖሚ አማካኝነት ባስቆጠራት ብቸኛ ግብ ባለሜዳውን ሲዳማ ቡናን በማሸነፍ ከሜዳው ውጭ በዘንድሮው የሊግ ጨዋታ 2ኛ ድሉን አስመዝግቧል፡፡
በክልል ስታዲዬሞች ከተካሄዱ ጨዋታዎች መካከል ይርጋለም ላይ ኢትዮጽያ ቡናን ከሲዳማ ቡና ያገናኘው ጨዋታ በሁለተኛው የጨዋታ አጋማሽ በደጋፊዎች ረብሻ ለ11 ደቂቃዎች ጨዋታው እንዲቋረጥና እንዲቀጥል በተደረገበት ጨዋታ እንግዳው ኢትዬጵያ ቡና ድል ቀንቶታል፡፡
በቡና ደርቢ ጨዋታ በይርጋለም ስታዲዬም በሁለቱም ቡድኖች በኩል ተመጣጣኝ ፍክክር በተስተናገደበት ጨዋታ ሁለቱም ቡድኖች ጨዋታውን በአሸናፊነት ለማጠናቀቅ የነበራቸው ፍላጎትና ሜዳ ላይ ያሳዩት እንቅስቃሴ ለተመልካች ማራኪ ነበር፡፡በጨዋታው መጀመሪያ የግብ ዕድል በመፍጠር በኩል ቀዳሚዎቹ ባለሜዳዎቹ ሲዳማዎች ነበሩ፡፡ ሲዳማ ቡና ገና ጨዋታው ከመጀመሩ በ1ኛ ደቂቃ በአድስ ግዳይ አማካኝነት የግብ ዕድል ቢፈጥሩም ሳይጠቀምበት ቀርቷል፡፡
በጨዋታው እንግዳዎቹ ኢትዮጵያ ቡናዎች ኳስን መስርተው አልፎ አልፎ በረጅሙ ለአጥቂ ክፍሉ በሚጣሉ ኳሶች የግብ ዕድል ለመፍጠር ቢጫዎቱም ያን ያህል የሚባል አልነበረም።ነገር ግን በ42ኛው ደቂቃ የእንግዳዎቹ አጥቂ ሳሙኤል ሳኑሚ የሲዳማውን ግብ ጠባቂ መሳይን አታሎ ካለፈ በውሃላ ወደ ግብ የመታት ኳስ ከመረብ ጋር አለመገናኘቷ የማይታመን ነበር፡፡ባለሜዳዎቹ በመስመር ጥቃት ለመሰንዘር ቢሞክሩም ከሀሳብ ያለፈ አልነበረም፡፡
በሁለተኛው የጨዋታ አጋማሽ በአንፃራዊነት የተሻሉ የነበሩት ባለሜዳዎቹ ሲዳማ ቡናዎች ብዙ የጎል ዕድል ቢፈጥሩም የሚደረጉት የግብ ሙከራዎች በተደጋጋሚ በኢትዮጵያ ቡናው ግብ ጠባቂ ሀሪሰተን አማካኝነት ሲመክኑ አምሽተዋል።
ሁለተኛው የጨዋታ አጋማሽ የመጀመርያውን 15 ደቂቃ ኢትዬጵያ ቡናዎች የተሻሉ ሲሆን በ 59ኛ ደቂቃ በመልሶ ማጥቃት የሄደውን ኳስ አስቻለው ግርማ ወደ ግብ ሞክሮ የተመለሰውን ኳስ አጠገቡ የነበረው ሳሙኤል ሳኑሚ ወደ ግብነት ለውጧል።ከግቧ መቆጠር በኅላ ግብ ጠባቂው መሳይ አያኖ ተጎድቶ ሲውጣ እሱን ተክቶ ፍቅሩ ወደሳ ወደ ሜዳ መግባት ችሏል።
ከግቧ መቆጠር በኃላ በ63ኛ ደቂቃ ላይ በደጋፊዎች አከባቢ በተፈጠረው ረብሻ ጨዋታው ለ 11 ደቂቃ ተቋርጦ ከቆዬ በሇላ ከ 11 ደቂቃ በኅላ ጨዋታው እንዲቀጥል ተደርጓል።የባለሜዳዎቹ የሲዳማ ቡና ደጋፊዎች በቡድናቸው አቋም ተቃውሞ ሲያሰሙ ተደምጧል።
በቀሪዎቹ 30 ደቂቃዎች ሲዳማ ቡና የተሻለ እንቅስቃሴ ሲያደረጉ የግብ ዕድል በመፍጠርም የተሻሉ ነበሩ፡፡በአዲስ ግዳይ ሁለት ጊዜ ከ ሀሪሰን ጋር ብቻውን ቢገናኝም ዛሬ ጥሩ ያልነበረው አዲስ ግድይ ሳይጠቀምበት ቀርቷል።
የአሰልጣኞች አሰተያየት
ዘርኣይ ሙሉ -ሲዳማ ቡና
” በመሸነፋችን ይቅርታ እየጠየኩ ነው፡፡በተመዘገበው ውጤቱ ደጋፊዎች ተበሳጭተዋል፡፡በመሆኑም በቀጣይ ጨዋታ ላይ የአሰላለፍ ቅያሪ በማድረግ በቅርቡ ወደ ውጤት እንመለሳለን፡፡”
ዲዲዬ ጎሜዝ- ኢትዮጵያ ቡና
“ማሸነፋችን የመልካም ስራ ውጤት ነው ድላችን ይቀጥላል ፡፡በቀጣይም ተጋጣሚዎቻችን ለማሸነፍ ጠንክረን እንሰራለን፡፡”
አስተያየት ይስጡ